የጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ እስራት መቀነስ
ሰኞ፣ ሐምሌ 30 2004ፍ/ቤቱ ቅጣቱን ያሻሻለው በጋዜጠኛዋ ላይ የተመሰረቱትን 2 ክሶች ውድቅ ካደረገ በኋላ ነው ። ስለ ተሻሻለው የፍርድ ውሳኔ የርዕዮት አሉሙን ጠበቃ አቶ ሞላ ዘገየን እና በአለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት በእንግሊዘኛው ምህፃር CPJ የምስራቅ አፍሪቃ ጉዳዮች ተመራማሪ ቶም ሮድስን አነጋግረናል።
የርዕዮት ፍርዱ ዝቅ ሊል የቻለበትን ምክንያት የርዕዮት አሉሙ ጠበቃ አቶ ሞላ ዘገየ ለዶቼቬለ ተናግረዋል። ወ/ት ርዕዮት አሁን የቀረባት ክስ በቀጥታና በተዘዋዋሪ ከአሸባሪዎች ጋር ተባብረሻል የሚለው ክስ እንደሆነ ጠበቃዋ ገልፀዋል። ርዕዮት በመጀመሪያው ፍርድ ፅኑ እስራት ብቻ ሳይሆን የ33 ሺሕ ብር የገንዘብ ቅጣትም ተበይኖባት ነበር። አቶ ሞላ መልስ ሰተውናል።
አለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት በእንግሊዘኛ ምህፃሩ CPJ የኢትዮጵያ ፌደራል ጠቅላይ ፍ/ቤት በጣለው ብይን ላይ በበኩሉ አስተያየት ሰተዋል። የድርጅቱ የምስራቅ አፍሪቃ ጉዳዮች ተመራማሪ ቶም ሮድስ « ግልፅ ነው ፍርዱ በመቀነሱ ደስተኛ ነን። ግን አሁንም አንዳችም ደቂቃ በፍርድ ቤት መቆየት አይገባትም ብለን እናስባለን። ምክንያቱም ያጠፋችው ስህተት የለምና። እኛ እንደሚመስለን ጠንካራ ተቺ አስተያየቶች መፃፍ የአሸባሪነት ድርጊት ከተባለ በኢትዮጵያ የፕረስ ነፃነት የሚገኝበት ደረጃ እና መተቸት መቻል ለኛ እንደ በፊቱ የሚያስቀጣ ነው ። ይህን ነው በርዕዮት አለሙምጉዳይ የሚታየው ።»
ቶም ሮድስ አክለው እንዳሉት የርእዮት እሥራት መቀነስ በእስር ላይ በሚገኙ እንደ እስክንድር ነጋ በመሳሰሉ አምደኞች ላይ የተላለፈው ፍርድ በድጋሚ እንዲታይ ተስፋ ሰጪ ይሆናል።
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ