1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የግሪክ ፖሊስ ኢዶሚኒን ማስለቀቅ ጀመረ

ማክሰኞ፣ ግንቦት 16 2008

የግሪክ ፖሊስ ሐገሪቱን ከመቂዶንያ ጋር በሚያዋስነዉ ኢዶሚኒ በተባለዉ አካባቢ ሰፍረዉ የሚገኙ ሥደተኞችን ማስለቀቅ ጀመረ። ኢዶሚኒ ላይ ሰፍረዉ የሚገኙት ስደተኞች ወደ መሃል አዉሮጳ የሚገቡበት የባልካን መንገድ ዳግም ተከፍቶ በቀጣይ መጓዝ እንችላለን በሚል ተስፋ ትናንሽ ድንኳን ተክለዉ ይኖሩ ነበር።

https://p.dw.com/p/1ItlR
Griechenland Behörden beginnen mit Räumung des Flüchtlingslagers in Idomeni
ምስል Reuters/Y. Kolesidis

የነዚህ ስደተኞች ቁጥር ወደ 9000 እንደሆነም ተዘግቦአል። ሊስ ቦታዉ ላይ በድንኳን ሰፍረዉ የነበሩትን ስደተኞች ለማስለቀቅ በደረሰ ጊዜ ተሰብስበዉ የነበሩ ጥቂት ሰዎች ለማስተጓጎል ሞክረዉ ነበር። በኢዶሚኒ የሚታየዉን የስደተኞች ቀዉስን በተመለከተ ግሪካዊዉ ጊዮርጎስ ኬርቲሲስ ለጀርመን መገናኛ ብዙኃን እንደገለፁት ስደተኞች ስፍረዉበት የሚገኘዉን ኢዶሚኒን ለማስለቀቀ በርከት ያሉ ቀናቶች ይወስዳል። የማስለቀቁ ሥራም ጉልበት ያልቀላቀለዉ እንዲሆን ይሞከራል። በኢዶሚኒ ድንኳን ዉስጥ ሰፍረዉ የሚገኙት ሰዎች ወደ ተስተካከለ መኖርያ ቦታ እንደሚወሰዱም ተመልክቶአል። ቦታዉ ላይ የሚገኝ የዶቼ ቬለ ጋዜጠኛ ሶሊቨር ሳሊት፤ ቦታዉ ለጋዜጠኞችም ዝግ መሆኑን ገልጾአል።

Griechenland Idomeni Flüchtlinge vor Bussen
ምስል Reuters/O. Teofilovski

«ወደ ኢዶሚኒ የሚወስድ የፈጣን ተሽከርካሪ መሄጃ ጎዳና ይታየኛል። ስደተኞቹ እኔ ካለሁበት ቦታ እጅግ ርቀት ላይ ነዉ የሚገኙት፤ ጋዜጠኞች ከሁለት እስከ ሦስት ኪሎሜትር ርቀት ላይ ማለፍ አይችሉም ፤ ተዘግቶአል። ብዙ ባዶ አዉቶቡሶች ወደዝያ ሲያልፉ ይታየኛል፤ ከዝያም ሰዎችን የጫኑ አዉቶቡሶች ሲመለሱ ብቻ ነዉ የሚታየዉ። እንደሚመስለኝ አዉቶቡሶቹ ወደ 9000 ሺህ የሚሆኑትን ስደተኞች ነዉ እያመጡ ያሉት። »

የግሪክ መገናኛ ብዙኃን ይፋ እንዳደረጉት ኢዶሚኒን ከስደተኞች ለማስለቀቅ ወደ 1400 ፖሊሶች ተሰማርተዉ ይገኛሉ። እንደ ዓይን እማኞች ጥቂት ስደተኞች አካባቢዉን በመልቀቅ አቅራብያዉ ወደ ሚገኘዉ ጫካ ተደብቀዋል። ሌሎች ያለምንም ኃይልና ትዕዛዝ በገዛ ፈቃዳቸዉ ወደ ሚወሰዱበት ቦታ ተነስተዉ ሄደዋል። አብዛኞች በገዛ ፈቃድ የተነሱት ሰዎች ሕፃናትና ልጆችን የያዙ መሆናቸዉ ተዘግቦአል።

አዜብ ታደሰ

ነጋሽ መሐመድ