1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የግብፅ ፖለቲካዊ ቀዉስና ዲፕሎማሲዉ

ሐሙስ፣ ሐምሌ 25 2005

የግብፅ ጦር የሰየመዉ ጊዚያ መንግሥት ግን ጥሪ ማሳሰቢያዉን የተቀበለዉ አይመስልም።የጊዚያዊ መንግሥቱ ካቢኔ መፈንቅለ መንግሥቱን በመቃወም በሁለት አደባባዮች የከተመዉን ሕዝብ «ለሐገሪቱ ፀጥታ አስጊ» እና «አሸባሪ» በማለት ወንጅሎታል።ፖሊስ ሕዝቡን ከሁለቱም አደባባዮች እንዲያባርርም አዟል።

https://p.dw.com/p/19IQ4
Egyptian supporters of the deposed president Mohamed Morsi hold his portrait and wave the national flags during a demonstration against the government in Cairo on July 31, 2013. Tense Egypt braced for a showdown in the streets between supporters of Morsi and his army-backed opponents, who have called for demonstrations across Egypt. AFP PHOTO/FAYEZ NURELDINE (Photo credit should read FAYEZ NURELDINE/AFP/Getty Images)
ተቃዉሞዉምስል Fayez Nureldine/AFP/Getty Images
Außenminister Guido Westerwelle (l, FDP) spricht neben seinem ägyptischen Amtskollegen Nabil Fahmy am 01.08.2013 während einer Pressekonferenz im Außenministerium in Kairo in Ägypten. Westerwelle hält sich zu politischen Gesprächen in Kairo auf und will unter anderem mit dem Präsidenten der Übergangsregierung Mansur zusammentreffen. Foto: Michael Kappeler/dpa pixel
ዲፕሎማሲዉ፤ ቬስተርቬለና ፋሕሚምስል picture-alliance/dpa
„Ägypten: Zerstört der Krieg gegen Terrorismus Demokratie?„ einstellen? Die Bilder haben wir von unserem Korrespondenten in Ägypten Ahmed Wael bekommen. (S. e-mail unten). Stichwörter für alle Bilder: Ägypten, Krieg, Terrorismus, Islamisten, Demokratie, Muslimbrüder.
ተቃዋሚዉን ለመቆጣጠር-ታንክምስል Ahmed Wael

የግብፅ ደም አፋሳሽ ፖለቲካዊ ዉዝግብ ሠላማዊ መፍትሔ እንዲያገኝ የሚደረገዉ ዓለም አቀፋዊ ዲፕሎማሲ እንደቀጠለ ነዉ።የአዉሮጳ ሕብረት እና የአፍሪቃ ሕብረት መልዕክተኞች ካይሮ ደርሰዉ ሲመለሱ የጀርመን ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ደግሞ ትናንት ማታ ካይሮ ገብተዋል።ዩናይትድ ስቴትስ ሁለት አንጋፋ ሴናተሮቿን ወደ ካይሮ እንደምትልክ አስታዉቃለች።እዚያዉ ካይሮ ዉስጥ ግን የግብፅ ጦር የሰየመዉ የጊዚያዊ መንግሥት ባለሥልጣናት እና ጦሩ በመፈንቅለ መንግሥት ከስልጣን ያስወገዳቸዉ የቀድሞዉ ፕሬዝዳት ደጋፊዎች ማስጠንቀቂያና ዛቻ እንደተካረረ ነዉ።

ዓለምን ካስደነቀ ሕዝባዊ ሠላማዊ ሠልፍ እና ምርጫ፥ ባጭር ጊዜ ሕይወት፥ ደም አካልን ካጠፋ ግጭት፥ቁርቁስ ተዘፍቃለች።ግብፅ።ፀጥታ አስከባሪዎች ባለፈዉ ቅዳሜ ያልታጠቁ ሠልፈኞችን ደረት ጭንቅላታቸዉን እየፈለሱ መግደል፥ ማቁሰላቸዉ ደግሞ ዉዝግብ ግጭት፥ ቁርቁሱ የዚያችን ሐገር የወደፊት ጎዞ መንታ መንገድ ላይ አድርሶታል።


ሁለቱም ጥሩ አይደለም።የፖለቲካ ታዛቢዎች እንደሚሉት አንድም ከፈጠጠ ወታደራዊ አገዛዝ አለያም ከለየለት የርስ በርስ ጦርነት የሚያደርስ-መጥፎ መንገድ።በሕዝብ በተመረጡት ፕሬዝዳት በመሐመድ ሙርሲ ላይ የተደረገዉን መፈንቅለ መንግሥት በመቃወም አደባባይ የወጡ ሠልፈኞችን ፀጥታ አስከባሪዎች መግደል፥ ማቁሰላቸዉ ያስደነገጠዉ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ከሁለቱ መጥፎ መንገዶች ሌላ-ሰወስተኛ አማራጭ እንዲፈልግ እየጠየቀ ነዉ።

በትንሽ ግምት ሰማንያ-ሁለት ሰልፈኞች በተገደሉ፥ በሺሕ የሚቆጠሩ በቆሰሉ በሳልስቱ ሰኞ ካይሮ የገቡት የአዉሮጳ ሕብረት የዉጪ ግንኙነት ሐላፊ ወይዘሮ ካትሪን አሽተን ግብፆችን ለማረጋጋት እና ሰወስተኛ አማራጭ ለመጠቆም የመጀመሪያዋ ናቸዉ።

«ሁከት ሥፍራ እንደሌለዉ እና ሠላማዊ የተቃዉሞ ሠልፍ አስፈላጊ መሆኑን ግልፅ አድርገናል። በተገቢዉ መንገድ መደረጉ ግን መረጋገጥ አለበት።»

አሽተን እስረኛዉን ፕሬዝዳት ማነጋገራቸዉንም አስታዉቀዋል።መፈንቅለ መንግሥቱን በመቃወም ግብፅን ከአባልነት ያገለለዉ የአፍሪቃ ሕብረት ወደ ካይሮ የላካቸዉ መልዕክተኞችም ትናንት ሙርሲን ማነጋገራቸዉን አስታዉቀዋል።የቀድሞዉ የማሊ ፕሬዝዳት አልፋ ዑመር ኮናሬ የመሩት የአፍሪቃ ሕብረት የመልዕክተኞች ጓድ እንደ አዉሮጳ ሕብረት ሁሉ ግጭት ሁከቱ በሠላማዊ መንገድ እንዲፈታ ከማሳሰብ የተለየ መልዕክት አላስተላለፈም።


የግብፅ ጦር የሰየመዉ ጊዚያ መንግሥት ግን ጥሪ ማሳሰቢያዉን የተቀበለዉ አይመስልም።የጊዚያዊ መንግሥቱ ካቢኔ መፈንቅለ መንግሥቱን በመቃወም በሁለት አደባባዮች የከተመዉን ሕዝብ «ለሐገሪቱ ፀጥታ አስጊ» እና «አሸባሪ» በማለት ወንጅሎታል።ፖሊስ ሕዝቡን ከሁለቱም አደባባዮች እንዲያባርርም አዟል።

ካቢኔዉ በዚሕ አላበቃም።የተቃዋሞ ሠልፉን የሚያደራጀዉ የሙስሊም ወንድማማቾች ማሕበር መሪዎች የተያዙት ሕዝብን ለአመፅ በማነሳሳት ወንጀል እንዲከሰሱ፥ ያልተያዙት ታድነዉ እንዲታሰሩ አዟል።ተቃዋሞ ሠልፈኛዉም «እጅ አንሠጥም» ባይ ነዉ-«እንሞታለን እንጂ።»

Catherine Ashton / EU / Europäische Union (Foto: AP)
አሽተንምስል AP

«ፕሬዝዳንቱን ወደ ሥልጣን ከመመለስ ሌላ፥ ሌላ መፍትሔ ይገኛል ብለን አንጠብቅም።ፕሬዝዳንቱ አንድም በፖለቲካዊ ድጋፍ አለያም በድርድር ወደ ሥልጣን (መመለስ (አለባቸዉ)።ይሕ ካልሆነ ግን ተጨማሪ ደማችንን እናፈሳለን።ደማችን ብዙ በፈሰሰ ቁጥር የግብፅ ሕዝብ አላማችንን ተገንዝቦ እኛን ይቀየጣል።»ይላሉ ከተቃዋሚ ሠልፈኞቹ አንዱ።

የጀርመኑ ወጪ ጉዳይ ሚንስትር ጊዶ ቬስተርቬለ ዛሬ የጊዚያዊ መንግሥቱን ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ነቢል ፈሕሚን ጨምሮ ከተለያዩ ባለሥልጣናት ጋር ተነጋግረዋል።ጀርመናዊዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር የግብፅ ጦር የሾማቸዉ ፖለቲከኞችና የተቃዋሚዎቻቸዉን ጠብ ዉዝግብ ለማብረድ የፈየዱት መኖር አለመኖሩ በግልፅ አልታወቀም።

ቬስተርቬለ በሙርሲ ላይ የተደረገዉን መፈንቅለ መንግሥት በግልፅ በመቃወም የመጀመሪያዉ የምዕራባዊ ሐገር ትልቅ ባለሥልጣን ነበሩ።

«ለግብፅ ዴሞክራሲ ከባድ ቅልበሳ ነዉ።አሁን በጣም አስፈላጊዉ ነገር ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት ዳግም የሚመሠረትበትን መንገድ ማፈላለጉ ነዉ።ሁሉም ባለጉዳዮች ከሐይል እርምጃና ከሁከት እንዲታቀቡ እንጠይቃለን።»

የያኔዉን መልዕክት ካይሮ ላይ አድማጭ ማግኘቱ አጠራጣሪ ነዉ።ያም ሆኖ ከመፈንቅለ መንግሥቱ በሕዋላ ካይሮን ለመጎብኘትም ቬስተርቬለ የመጀመሪያዉ የምዕራባዊ ሐገር ትልቅ ዲፕሎማት ሆነዋል።ዩናይትድ ስቴትስም ሁለት ሴናተሮቿን ወደ ካይሮ ለመላክ ወስናለች።

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ





ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ