የፆታዎች እኩል የሥራ ምደባ በአውሮፓ
ማክሰኞ፣ የካቲት 5 2005ክፍላተ ሃገር ተወካዮች ምክር ቤት በጀርመን አሠራሩ ተግባራዊ እንዲሆን ተስማምቷል ። የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን በአውሮፓ ትላልቅ ኩባንያዎች ቦርዶች ውስጥ የሴቶችና የወንዶች አባላትን ቁጥር ለማመጣጠን ይረዳል ያለውን ረቂቅ ህግ ካፀደቀ 3ተኛው ወር እየተገባደደ ነው ። በዚህ ረቂቅ ህግ መሠረት በአውሮፓ ህብረት አባል ሃገሮች ውስጥ የተመዘገቡ ትላልቅ ኩባንያዎች እ.ጎ.አ እስከ 2020 ድረስ ሥራቸውን ከሚቆጣጠሩት የቦርድ አባላት ቢያንስ 40 በመቶው ሴቶች መሆን ይኖርባቸዋል ። በአውሮፓ ህብረት የፍትህ ጉዳዮች ኮሚሽነር ቪቭያን ሬዲንግ የቀረበው ይኽው ረቂቅ ፣ ኩባንያዎች የቦርድ አባልነት ክፍት የሥራ ቦታ ተገቢው የሙያ ብቃት ላላው ሆኖም በበቂ ሁኔታ ላልተወከለው ፆታ እንዲሰጥ ያስገድዳል ። ሬዲንግ ያቀረቡት እቅድ በአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ውስጥ የተመዘገቡ ወደ 5 ሺህ የሚጠጉ ኩባንያዎችን ይመለከታል ። ሪዲንግ እቅዱን ያወጡበትን ምክንያት ዘርዝረዋል ።
« በአሁኑ ጊዜ ከዩኒቨርስቲ ምሩቃን 60 በመቶው ሴቶች መሆናቸው ሲታሰብ የሰዎችን ተሰጥኦ ዋጋ ቢስ ማድረግ ነው ። ተሰጥኦ ያላቸውን ሴቶች ከፍተኛ ደረጃ ያላቸውን ሥራዎች መያዝ የሚገድባቸውን ግድግዳና ጣሪያ ለማፍረስ ነው ይህን ህግ ዛሬ ያቀረብነው ። መመረጥ ያለባቸው ግን ብቃቱ ያላቸው ሴቶች ናቸው ። ይህ በጣም አስፈላጊ ነው ። ሴቶች በሴትነታቸው ብቻ በቦርድ ውስጥ የሥራ ቦታ ያግኙ ሳይሆን የሙያው ብቃት እስካላቸው ድረስ እኩል እድል ይሰጣቸው ነው ። »
የፆታዎች እኩል የሥራ ምደባ ተግባራዊ እንዲሆን የሚጠይቀው ረቂቅ ህግ አመታዊ ገቢያቸው ከ50 ሚሊዮን ዩሮ ወይም ከ 63.6 ሚሊዮን ዶላር የማይበልጥ እንዲሁም ከ 250 ያነሰ ሠራተኛ ያላቸውን ኩባንያዎች አይመለከትም ። ኮሚሽነር ሬዲንግ በአውሮፓ ሴቶች ከፍተኛ የሃላፊነት ቦታዎች እንዲያገኙ የኮታ አሠራር ተግባራዊ እንዲሆን ሙከራ ሲያደርጉ የዛሬ 3 ወሩ ሙከራ የመጀመሪያቸው አይደለም ። ከ6 ወራት በፊትም ውድቅ የሆነባቸውን ሌላ ረቂቅ ህግ ለአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን አቅርበው ነበር ። የአሁኑ ረቂቅ ከቀደመው የሚለየው ህጉን በማያከብሩ ሃገራት ላይ የሚጣለው ማዕቀብና ቅጣት መቀነሱ ነው ። ኮሚሽነር ሬዲንግ ይህን ረቂቅ ህግ ያወጡት የአውሮፓ ኩባንያዎች አሠራሩን በፈቃደኝነት መተግበር ስለተሳናቸው መሆኑን አስታውቀዋል ። ሪዲንግ እንዳሉት በጎርጎሮሳውያኑ 2011 አ.ም የሴት የቦርድ አባላት ቁጥር በጥቂቱ ነው የጨመረው ። በ 2011 በአውሮፓ ኩባንያዎች ቦርዶች ውስጥ የሴቶች ቁጥር በመቶኛ ሲሰላ በአማካይ 13.5 በመቶ ይጠጋል ። ሬዲንግ እንዳሉት ረቂቁ በ 2 መንገዶች ተግባራዊ ሊሆን ይችላል ።
« ህጉን ተግባራዊ ማድረጊያው አንደኛው መንገድ እጎአ ከ2016 ጀምሮ እኔ ነክሰው የሚይዙ ብዮ የምጠራቸው ማዕቀቦች በብሔራዊ ህግ ውስጥ እዲካተቱ ማድረግ ነው ። ሁለተኛው አባል ሃገሮች ህግን በመጣስ ግዴታቸውን ካልተወጡ የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን እርምጃ መውሰድ ይጀምራል »
ካሚሽነሯ ያቀረቡት ረቂቅ ህግ ከአውሮፓ ህብረት ሴት ከፍተኛ ባለሥልጣናትና ከአባል ሃገራት ፖለቲከኞች በኩል ተቃውሞ ተነስቶበታል ። ከተቃዋሚዎቹ መካከል የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳዮች ሃላፊ ካትሪን አሽተን ና የህብረቱ የሃገር ውስጥ ጉዳዮች ኮሚሽነር ስዊድናዊቷ ሴሲልያ ማልስቶርም ይገኙበታል ። በአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ውስጥ በፆታዎች እኩል ምደባ ረገድ ተመሳሳይ አሠራር የለም ። የኮታ አሠራርን ተግባራዊ ያሚያደርጉ አንዳንድ የስካንድኔቪያን ሃገሮች ሲኖሩ በነዚህ ሃገራትም አሉታዊ ውጤት ማስከተሉን ነው የአሠራሩ ተቃዋሚ የሆኑት አስትሪድ ሉሊንግ በአውሮፓ ፓርላማ EBP በሚል ምህፃር የሚታወቀው የኖርዌይ የወግ አጥባቂ ፓርቲ የወግ አጥባቂው ፓርቲ ተወካይ
ያስረዱት
« ህጉ ከመውጣቱ በፊት ኖርዌይ ውስጥ ከ 600 በላይ የአክስዮን ኩባንያዎች ነበሩ ከ 3 አመት በኋላ 3 መቶ ሺ ያህል ገደማ ነው የቀሩት ። አብዛኞቹ እንደሚሉት የዚህ ምክንያቱ የሴቶች እኩል የስራ ምደባ ጥያቄ ነው ። »
ሉሊንግ እንደሚሉት በቀደሙት ጊዜያት በተወሰኑ የሙያ መስኮች ውስጥ የሚሰማሩ ሴቶች ቁጥር አነስተኛ የሆንበት ምክንያት ለከፍተኛ ሃላፊነት በሚያበቁ ሙያዎች ባለመሠልጠናቸው ነው ።
« በመጀመሪያ ማየት የሚቻለው ሴቶች የተለያየ የሙያ ዘርፎችን መምረጥ እንደሚችሉ ነው ። ያም ሆኖ በአብዛኞቹ አገሮች ማዕከላዊ ባንኮች አስተዳደር ውስጥ ሴቶች የሉበትም ምክንያቱም ቀደም ባሉት ጊዜያት ሴቶች ሂሳብ ፣ ፊናንስ ወይም የንግድና የኤኮኖሚ አስተዳደር ትምህርት አይከታተሉም ነበር ። እናም በዚሁ ዘርፍ የሃላፊነትን ቦታ ለማግኘት ከሞላ ጎደል ከባድነቱ የታወቀ ነው ። »
ሉሊንንግ ናሌሎችም የኮታ አሠራርን የሚቃወሙ ወገኖች የፆታዎች እኩል የሥራ ምደባ አለ አግባብ ጥቅም ላይ እንዳይውል ስጋት አላቸው ። ይሁንና ይህ አውሮፓ ህብረት የምጣኔ ሃብት ኮሚሽነር ኦሊ ሬን ዘንድ ተቀባይነት የለውም ። በርሳቸው አስተያየት የተመጣጠነ የፆታዎች ምደባ ባለባቸው መስሪያ ቤቶች ውጤታማ ሆነዋል ።
« የፆታዎች እኩል ምደባ አሠራር ተግባራዊ በሆነባቸው ኩባንያዎች የተሻለ የኤኮኖሚ አፈፃፀም ደረጃ ላይ ይገኛሉ ። በሥራ ቦታዎች የሴቶችንና የወንዶችን ቁጥር ለማመጣጠን በሚያደርጉት ጥረትም በልዩ ልዩ ወገኖች አክብሮት እየተሰጠ ነው ።
ረቂቁ ህግ ሆኖ ሥራ ላይ እንዲውል በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ና በ27 ቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት መሪዎች ተቀባይነት አግኝቶ መፅደቅ ይኖርበታል ። ረቂቁ ከስዊድንና ከብሪታኒያ መንግሥታት በኩል ከፍተኛ ተቃውሞ እንደሚገጥመው ይጠበቃል ። ኩባንያዎች ቦርዶች አባላት 16 በመቶው ብቻ ሴቶች በሆኑበት በጀርመን የኮታው አሠራር ገቢራዊ እንዲሆን የጀርመን ፌደራል ክፍላተ ሃገር ተወካዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ወስኗል ። የምክር ቤቱ እርምጃ የመራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል መንግሥት የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን ላቀረበው ረቂቅ ህግ ድጋፍ እንዲሰጥ ግፊቱን አጠናክሯል ። በአውሮፓ ፓርላማ የጀርመን የአረንጓዴው ፓርቲ ተወካይ ሬቤካ ሃርምስ የኮታው አሠራር ደጋፊ ናቸው
« በእኔ ግምገማ መሠረት እዚህ ላይ እኩል መብት በመሠረታዊ ህገ መንግሥትና በሰብአዊ መብት አዋጅ መገለፅ አለበት ። ይሁንና ይህን ተግባራዊ ለማድረግ ህግና ደንብ ያስፈልጋል እናም እንደኔ አስተሳሰብ የፆታዎች እኩል ደርሻ ወሳኝነት ያለው ነው »
ከፍተኛ የሃላፊነት ቦታዎች የሚሰጣቸው ሴቶች ቁጥር ከፍ እንዲል የአውሮፓ ፖለቲከኞች የሚያቀርቡት ጥሪ ቀጥሏል ። አባል ሃገራትም ህጉን ተቀብለው ከማፅደቃቸው በፊት ከኮሚሽኑና ከአውሮፓ ፓርላማ ጋር በረቂቁ ላይ መምከራቸውን ይቀጥላሉ ። አውሮፓውያን በጉዳዩ ላይ የሚካሄደው ክርክርም በየአቅጣጫው እንደቀጠለ ነው ።
ሂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ