1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የፎልክስ ቫገን ሥራ አስኪያጅ ሥልጣን ለቀቁ

ረቡዕ፣ መስከረም 12 2008

ዛሬ የፎልክስ ቫገን የቦርድ አባላት በቅሌቱና በኩባንያው የወደፉት እጣ ፈንታ ላይ ለመነጋገር በተሰብስቡበት መሃል ነበር ስራ አስኪያጁ ሥልጣን መልቀቃቸው የተነገረው ።

https://p.dw.com/p/1Gc6T
Deutschland - Volkswagen Martin Winterkorn
ምስል Getty Images/S. Gallup

በማጭበርበር ቅሌት ከፍተኛ ወቀሳ የተሰነዘርበት የጀርመኑ የመኪና አምራች ኩባንያ ፎልክስ ቫገን ዋና ስራ አስኪጅ ማርቲን ቪንተርንኮርን ዛሬ ሥልጣን ለቀቁ ።ስራ አስኪያጁ ኩባንያቸው ላደረሰው ጥፋት ትናንት በይፋ ይቅርታ ጠይቀው ነበር ። ይሁንና ይቅርታ በጠየቁበት መልዕክታቸው ትልቁን የአውሮፓ መኪና አምራች ኩባንያ ከመምራት ሃላፊነታቸው የመውረድ ፍንጭ አላሳዩም ነበረ ። ዛሬ የፎልክስ ቫገን የቦርድ አባላት በቅሌቱና በኩባንያው የወደፉት እጣ ፈንታ ላይ ለመነጋገር ተሰብስበው ነበር ።ስራ አስኪያጁ ሥልጣን መልቀቃቸው የተነገረው በስብስባው መሃለ ነበር ።በሌላ በኩል የጀርመን አቃቤ ህግ ፣በፎልክስ ቫገን የማጭበርበር ቅሌት ላይ የመጀመሪያ ደረጃ የወንጀል ምርመራ መጀመሩን አስታወቋል ። የብሩንስቪክ አቃቤ ህግ ፎልክስ ቫገን በናፍጣ በሚሰሩ መኪናዎች ላይ የተጭበረበረ የአየር ብክለት መቆጣጠሪያ ስለ መግጠሙ በኩባንያው የአስተዳደር ሃላፊዎች ላይ ምርመራ ለማካሄድ ማሰቡን ተናግረዋል ።ቪንተርንኮርን ኩባንያቸው ያጋበሰው ትርፍ ተጠቃሚ ሊሆኑ እንደሚችሉ ግልጽ ነው ይላሉ በአሜሪካው የካርኔጅ የጥናትና በጎ አድራጎት ተቋም የመኪና ሞተር ጉዳዮች አዋቂ ዴቦራ ጎርደን
« ፎልክስ ቫገን ባለፉት ዓመታት እየተስፋፋና ገቢውም እየጨመረ ሲሄድ በተለይ እርሳቸው ያገኙትን ጥቅምና የተጋሩትን ለይቶ ማወቁ ለፍትህ ሚኒስቴር ቀላል ነው ። ይሄ በኩባንያዎች አሠራር ውስጥ የተለመደ ነው ።»
። 11 ሚሊዮን የሚደርሱ በናፍታ የሚሰሩት መኪናዎቹ የብክለት ምርመራን ማለፍ የሚያስችል የተጭበረበረ ሶፍትዌር እንደተገጠመላቸው ያመነው ከዓለም ግዙፉ የመኪና አምራች ፎልክስ ቫገን ከፍተኛ የህግ መጣስ ክሶች እንደሚጠብቁት ይገመታል ። የአሜሪካን የአካባቢ ጥበቃ መሥሪያ ቤት በኩባንያው ላይ የ18 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ሊያስከትል የሚችል ምርመራ በማካሄድ ላይ ነው ።

Deutschland Volkswagen Auspuff Abgase Martin Winterkorn
ምስል picture-alliance/dpa/M. Murat

ኂሩት መለሰ

ነጋሽ መሀመድ