ዩክሬንና የአውሮፓ ህብረት
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 1 2006
መንግሥት በበኩሉ ውሉ ከመፈረሙ በፊት ከሩስያ ጋር የምማከርበት ፋታ ስጡኝ እያለ ነው ። ሩስያ ደግሞ የአውሮፓ መንግሥታት በዩክሬን ውሳኔ ጣልቃ መግባት የለባቸውም ስትል ታሳስባለች ። የአውሮፓ ህብረትና ሩስያ ዩክሬንን ወደ ራሳቸው ለመሳብ በየበኩላቸው የሚያካሂዱት ትግልና ከሁለት ወገን የተወጠረችውን የዩክሬን ወቅታዊ ሁኔታ የዛሬው አውሮፓና ጀርመን ዝግጅታችን ትኩረት ነው ። ለቅንብሩ ኂሩት መለሰ
ካለፉት 2 ሳምንታት ወዲህ የዓለምን ትኩረት የሳበችው ምሥራቅ አውሮፓዊቷ አገር ዩክሬን የ46 ሚሊዮን ህዝብ መኖሪያ ናት ። በዓለም ባንክ መመዘኛ መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሃገራት ተርታ ትመደባለች ። ከህዝቧ 77.8 በመቶው ዩክሬናውያን ፣ 17 በመቶው ሩስያውያን የተቀሩት ደግሞ ቤላሩሳውያንና ሮሜንያውያን ናቸው ። በቆዳ ስፋትዋ ከአውሮፓ ትልቁን ስፍራ ትይዛለች ። 603,628 ስኩዌር ኪሎሜትር የቆዳ ስፋት አላት። በስተምሥራቅና በስተሰሜን ምሥራቅ የሩስያ ፌደሬሽን ፣በሰተሰሜን ምዕራብ ቤላሩስ ፣በስተምዕራብ ፖላንድ ስሎቫክያና ሃንጋሪ፣ በስተደቡብ ምዕራብ ፣ ሮሜንያና ሞልዶቫ ፣በስተደቡብና በስተደቡብ ምሥራቅ ደግሞ ጥቁር ባህርና የአዞቭ ባህር ያዋስኗታል ። የዩክሬን ሶሻሊስት ሪፐብሊክ እጎአ 1922 የቀድሞዋን ሶቭየት ህብረት ከመሠረቱት ሪፐብሊኮች አንዷ ናት ። በ1941 በናዚ ጀርመን ተወራ በሩስያ ጦር ድጋፍ በ1944 ነፃ ብትወጣም ። በጦርነቱ አሸናፊ ሶቭየት ህብረት ስር ከመሆን አላመለጠችም ።
ሶቭየት ህብረት እጎአ በ1991 ስትፈረካከስ ግን ራስዋን የቻለች አገር ሆነች ። ዩክሬን ከዚያን ጊዜ አንስቶ የነፃ ኤኮኖሚ መርህ ታራምዳለች ። ለም መሬት ያላት ዩክሬን የእህል ምርት ለዓለም ገበያ በማቅረብ 3 ተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ ሃገር ናት ። ዩክሬን በእርሻ ብቻ ሳይሆን በኢንዱስትሪ ምርቶቿም ታዋቂ ሃገር ናት ። ልዩ ልዩ ወታደራዊ ተሽከርካሪዎችና ከባድ የጭነት መኪናዎች ግዙፉ የመንገደኞችና የእቃ ማመላለሻ አውሮፕላን አንቶኖቭም ይመረትባታል ። ከአውሮፓ ከሩስያ ቀጥሎ በወታደራዊ ኃይል ሁለተኛን ደረጃን የምትይዝም ሃገር ናት ። የአብዛኛዎቹ ምርቶቿ ገበያ አውሮፓ ነው ። ሃገሪቱ የሚያስፈልጋት የኃይል አቅርቦት በተለይ የነዳጅ ዘይት ና የተፈጥሮ ጋዝ ፍጆታዋ በአብዛኛው የሚገኘው ከሩስያ በመሆኑ የሞስኮ ጥገኛ ናት ። 25 በመቶ የተፈጥሮ ጋዝ ከሃገር ውስጥ ስታገኝ ፣35 በመቶውን ከሩስያ የተቀረውን 40 በመቶው በሩስያ በኩል ከመካከለኛው እስያ ሃገራት ታስገባለች ። በሌላ በኩል ሩስያ ለምዕራብ አውሮፓ ከምታቀርበው የተፈጥሮ ጋዝ 85 በመቶው የሚያልፈው በዩክሬን በኩል ነው ። በኢንዱስትሪና በእርሻ ምርቷ የምትታወቀው ዩክሬን መሰረተ ልማትዋ የሚፈለገውን ያህል ያልዳበረ በሙስናና በቢሮክራሲ ስሟ የሚነሳም ሃገር ናት ።
ከ4 ዓመት በፊት ነበር የአውሮፓ ህብረት ፣ዩክሬንን ጨምሮ ከምስራቅ አውሮፓዎቹ አገራት ከአርሜንያ ። ከአዘርባጃን ከጆርጅያ ከሞልዶቫና ከቤላሩስ ጋር የጋራ ስምምነት የመዋዋል ሃሳብ ያቀረበው ። እነዚህ ሃገራት ዲሞክራሲያዊ ማሻሻያዎች ካደረጉ ህብረቱ በለውጡ ከሃገራቱ ጋር ነፃ ንግድ ለማካሄድና ና የገንዘብ ድጋፍ ለመስጠት ቃል ገባላቸው ። የታቀዱት አጋርነቶች ልዩ የትብብር ስምምነቶች የህብረቱን አባልነት ሳይጨምር ዜጎች ያለ ቪዛ ወይም መግቢያ ፈቃድ እንዲንቀሳቀሱ ማስቻል ፣ ቀረጥ ወይም ግብርን መቀነስን እንዲሁም የአውሮፓውያን ስነ ምግባሮች ተግባራዊ ማድረግን ይመለከታሉ ። በይፋ ባይገለፅም የህብረቱ ሌላው ዓላማ ሩስያ በምሥራቅ አውሮፓ ሃገራት ላይ ያላትን ጫና ለመገደብ ያሰበ ና ሕብረቱም ወደ ምሥራቅ ምን ያህል እንደሚስፋፋ የሚያስቀምጥ ነበር ። በእቅዱ መሠረት በጎርጎሮሳውያኑ ህዳር 29 ያኑኮቪች 900 ገፅ
ያለውን ውል በወቅቱ የአውሮፓ ህብረት ሊቀመንበር በሊትዌንያ ዋና ከተማ ቪሊንዩስ ከአውሮፓ ህብረት ጋር ሊፈራረሙ ቀጠሮ ተይዞ ነበር ። ይሁንና የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቪክቶር ያኑኮቪች በጎርጎሮሳውያኑ ህዳር 21 ከዚህ ቀደም ቃል የገቡለትን የስምምነቱን ፊርማ ላልተወሰነ ጊዜ ማስተላለፋቸውን አስታወቁ ። የያኑኮቪች ውሳኔ ዩክሬን ከአውሮፓ ህብረት ጋር እንድትቀራረብ የሚፈልጉትን ወገኖች አስቆጥቶ ለተቃውሞ አደባባይ አስወጣ ። ተጠናክሮ በቀጠለው ተቃውሞ አዲስ መንግሥት እንዲመሰርት የሚቀርበው ጥያቄ ቀጥሏል ። ዩክሬን ወደፊት የአውሮፓ ህብረት አባል የምትሆንበት መንገድ እንዲመቻች የሚፈልጉት እነዚሁ ወገኖች ወደ ውህደቱ የሚደረገው ጉዞ ያለ ፕሬዝዳንት ቪክቶር ያኑኮቪች መንግሥት እንዲሆን ጥያቄአቸውን ማቅረብ የጀመሩት ገና ከጅምሩ አንስቶ ነው ።
«ካቢኔው ከሥልጣን መውረድ አለበት በምጣኔ ሃብቱም ቢሆን አዲስ ህይወት መጀመር አለብን ። »
«መንግሥት ከሥልጣን ይወርዳል ብለን እንጠብቃለን ። እናሸንፋለን ምክንያቱም ከመጀመሪያው ቀን አንስቶ እስከ መጨረሻው እዚህ እንቆያለን ። እናሸንፋለን ብዬ አስባለሁ ። የአውሮፓ አካል መሆን እንፈልጋለን አውሮፓም ይረዳናል ።»
«መንገዱን በሙሉ መዝጋት ይኖርብናል ። አንድም ባለሥልጣን ወደ ሚኒስትሮች ካቢኔ ቢሮ እንዳይገባ ለማድረግ ከበስተኃላችን ያለውን መንገድ መዝጋት አለብን ። »
«ወንጀለኛውን ፕሬዝዳንት እቃወማለሁ ። በቴሌቪዥን 3200ህሪቭንያስ የዩክሬን ገንዘብ 388 ዶላር እንደምናገኝ ይናገራሉ ። ልነግርህ እችላለሁ ማንም ይህን ያህል ደሞዝ አያገኝም ። በየክፍለ ሃገሩ ህዝቡ የሚላስ የሚቀመስ የለውም ። »
በዋና ከተማይቱ ክየቭ ከሚገኘው ማድያን ከተባለው የነፃነት አደባባይ አንስቶ በሌሎችም ከተሞች ተቃውሞው በዚህ መልኩ ቀጥሎ በሳምንቱ መጨረሻ ተቃዋሚዎች የሌኒን ሐውልት እስከማፍረስ ደርሰዋል ። የዓለም የከባድ ሚዛን ቦክስ ሻምፕዮንና ተቃዋሚ ፖለቲከኛ ቪታሊ ክሊችኮ እንደሚለው ህዝቡ በአደባባይ ተቃውሞውን ለመግለፅ የወጣው በዩክሬን ሁኔታዎች ከድጡ ወደ ማጡ እየሆኑ በመሄዳቸው ነው ።
« ህዝቡ በየጎዳናው የወጣው ቅር ስለተሰኘ ነው ። መንግሥት ይቀያየራል ፤ ሚኒስትሮችም ይለዋወጣሉ ። ሃገሪቱ ያለችበት ሁኔታ ግን አልተለወጠም ። ይልቁንም እየተባባሰ ነው የሄደው ። ሙሰኝነት ስርዓት አልበኛነት ተባብሷል ።ስርዓቱን መለወጥ አለብን ። »
ተቃዋሚዎች ይህን ሲሉ የዩክሬን ፕሬዝዳንት ያኑኮቪች ግን ውሳኔዬ ሃገሬን የሚጠቅም እንጂ የሚጎዳ አይደለም ሲሉ ለማግባባት እየሞከሩ ነው ።
« ወደ ተወሳሰቡ ውሳኔዎች ላይ መድረስ ግድ ይለኛል ። ለዚህም ነው አንዳንዴ ሰዎች በተሳሳተ መንገድ እንዲረዱኝ የሚያደርጉ ውሳኔዎችን ለመውሰድ የምደፍረው ። ለዚህም ነው ዛሬ ህዝባችን በጥንቃቄ እንዲያደምጠኝ የምጠይቀው ። ዩክሬንና ህዝቦችዋን የሚጎዳ አንድም እርምጃ ፈጽሞ አልወስድም ። »
ከአውሮፓ ህብረት ጋር የትብብር ውል ይፈርማሉ ተብለው ይጠበቁ የነበሩት ያኑኮቪች ውሳኔያቸውን ያስቀየሯቸው የሩስያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን መሆናቸው ነው የሚነገረው ።ዩክሬን በምዕራባውያኑ እጅ ውስጥ እንዳትወድቅ ከፍተኛ ትግል የሚያደርጉት ፑቲን በጎሮጎሮሳውያኑ ህዳር 9 2013 ዓም ከዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቪክቶር ያኑኮቪች ጋር ሞስኮ አቅራቢያ በሚገኝ አንድ ወታደራዊ አውሮፕላን ማረፊያ ውስጥ ተገናኝተው ያካሄዱት ንግግር ያኑኮቪች ውሉ ከመፈረም እንዲያዘገዩ አድርጓቸዋል ነው የሚባለው ። ሰሞኑን ቻይናን የጎበኙት ያኑኮቪች ወደ ሃገራቸው ሲመለሱ እግረ መንገዳቸውን በሩስያዋ የሶቺ ከተማ ከፑቲን ጋር መክረዋል ። ያኑኮቪች እስካሁን ከሁሉም ወገን የተሻለ ስምምነት እየጠበቁ ነበር ። ከአውሮፓ ህብረት ጋር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቅ የነበረው ስምምነት አሁን ለመፍረሱ በይፋ የሚሰጠው ምክንያት የቀድሞዋ የዩክሬን ጠቅላይ ሚኒስትር ዩልያዋ ቲሞሼንኮ ከእስር አለመለቀቅ ነው ። የአውሮፓ ህብረት የቲሞሼንኮን መለቀቅ እንደ ቅድመ ግዴታ አስቀምጧል ። ያኑኮቪች ደግሞ የቀድሞዋን ተቀናቃኛቸውን ለመፍታት አልፈለጉም ። ባለፈው ሳምንት የተሰበሰበው የሃገሪቱ ፓርላማም ቲሞሼንኮ እንዲለቀቁ የሚጠይቀውን ረቂቅ ህግ አላፀደቀም ። ከዚህ በላይ ግን ዩክሬን ከህብረቱ ና ከሩስያ በኩል ቃል የተገባላት የገንዘብ ማማለያዎች ወሳኝ ድርሻ ነበራቸው ። እዳ ለተቆለለበት ለዩክሬን ፑቲን በድጎማ መልክ በቢሊዮኖች ዮሮ የሚቆጠር ገንዘብ ለመስጠት እዳዋንም ለመሰረዝ እና እቃዎቿንም ከቀረጥ ነፃ እንድታስገባ ቃል ገብተውላታል ። የአውሮፓ ህብረት ደግሞ ወደ 610 ሚሊዮን ዩሮ ወይም 827 ሚሊዮን ዶላር ብድር ለመስጠት ነው ያቀደው ። ከዚሁ ጋር የዓለም የገንዘብ ድርጅት በምህፃሩ IMF የ1 ቢሊዮን ዩሮ ያልተረጋጠ የብድር ተስፋ ሰጥቷት ነበር ። የዩክሬን መሪዎች ከዚህኛው ይልቅ የሩስያው ቃል ስቧቸዋል ።
ተንታኞች እደሚሉት ለሩስያ ዩክሬንን መያዝ ጂኦ ፖለቲካዊ ተፅእኖ ማድረግ መቻል ብቻ ሳይሆን ከብዙ ዓመታት በፊት የሩስያ ግዛት እምብርት የነበረችውን ሃገር መቆጣጠር ማለት ነው ። የአውሮፓ ህብረትና ሩስያ በሚቋምጡላት በዩክሬን ሰበብ ብራስልስና ሞስኮ ከ23 ዓመታት በፊት የነበረውን ዓይነት የቀዝቃዛው ጦርነት ስሜት ውስጥ የገቡ ይመስላል ። ለሰሞኑ ተቃውሞ መንግስት የወሰደውን እርምጃ ህብረቱና አባላቱ እየተቃወሙት ነው ። ከዚሁ ጋርም መንግሥት ውሳኔውን እንደገና ያጤነዋል የሚል ተስፋ እንዳላቸው እያሳወቁ ነው ። የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ሆሴ ማኑዌል ባሮሶ ።
«የዩክሬን ባለሥልጣናት ዲሞክራሲያዊ ነጻነቶችንና ሰልፍ የማድረግ መብቶችን እንዲያከብሩ በግልፅ ተናግረናል ። ከዚሁ ጋርም ተቃዋሚ ሰልፈኞች ከኃይል እርምጃ እንዲቆጠቡ ጥሪ አቅርበናል ። ርግጥ ነው ይህ የሆነው ብዙዎቹ ዩክሬናውያን ወደፊት ከአውሮፓ ጋር መዋሃድ የሚፈልጉ በመሆናቸው ነው ። በቪሊኑሱ ጉባኤ ቅር በመሰኘታቸው ነው ። ሆኖም ውይይቱ ይቀጥላል ብለን ተስፋ እናደርጋለን ።
«
ባለፈው ሳምንት ክየቭ የሄዱት የጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጊዶ ቬስተርለም የአውሮፓ ህብረት አሁንም ዩክሬንን እጆቼን ዘርግቶ ለመቀበል ዝግጁ መሆኑን አስታውቀዋል ። ቬስተርቬለ እንዳሉት ዩክሬን ስምምነቱን ብትቀበል ተጠቃሚ ናት
ድምፅ
ቬስተርቬለ በኪቭ ጉብኝታቸው ተቃዋሚዎች በተሰበሰቡበት አደባባይ ተገኝተው ነበር ። መንግሥታት በዩክሬን ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገቡ ሩስያ ማሳሰቢያ እየሰጠች ነው ። ከዚህ ቀደም በተለያዩ ጊዜያት ዩክሬን ጥገኛዋ መሆኗን ለማስረገጥ ሩስያ ልዩ ልዩ እርምጃዎች ወስዳባታለች ። 3 ጊዜያት የተፈጥሮ ጋዝ በማቋረጥ ኃይሏን አሳይታታለች ። አልፎ አልፎ የሩስያ ምርቶች እንዳይገቡም ማገዷ አልቀረም ። ዩክሬን ለውጭ ገበያ ከምታቀርበው ምርት አንድ ሶስተኛው ወደ ሩስያ የሚላክ ሲሆንወደ አውሮፓ ህብረት የምትልከው ደግሞ 25 በመቶ ብቻ ነው ። በነዚህ ምክንያቶች ዩክሬን ወደ ሩስያ ያደላች ይመስላል ። ከአውሮፓ ህብረት ጋር የምትፈራረመው ውል ለአንድ ዓመት እንዲዘግይ አድርጋለች ። በዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ የምትገኘው ዩክሬን የታሰበውን ውል ወደፊት መፈረሟ አጠራጣሪ ቢመስልም ህብረቱን ግን ምን ጊዜም በሩን ክፍት አድርጎ እንደሚጠብቃት ነው ያሳወቀው ።
ኂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ