ያገረሸው ግጭት በምዕራብ እና ማዕከላዊ ጎንደር ዞኖች
ሐሙስ፣ ጥር 30 2011በሰሜን ጎንድር ዞን በየወቅቱ ይነሳ የነበረውን ችግር ለመፍታት የአማራ ክልላዊ መንግስት በሶስት ዞኖች በማዋቀርና በዞኑ ይነሳ የነበረውን የማንነት ጥያቄ የፈታ ቢሆንም ግጭቱ ግን ሳይሻሻል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ መጥቷል፡፡ አንዴ ሞቅ አንዴ በረድ የሚለው የአካባቢው ችግር ሰሞኑን እንደገና አገርሽቶ ህይወት ጠፍቷል ንብረትም ወድሟል፡፡ በዚህም ምክንት ከመተማ ጎንደርና ባህር ዳር የሚወስደው አውራ ጎዳና በመዘጋቱ ህብረተሰቡ ለከፍተኛ ወጪ ተዳርጓል፡፡ ጎንደርና ባሕር ዳር ለመድረሰም በኢትዮጵያ ሱዳን ጠረፍ በመዞር ረጅምና አድካሚ ጎዞ በማድረግ ግድ እንደሆነባቸው አንድ በምዕራብ ጎንር ዞን የመተማ ከተማ ነወሪ ለ “DW” የተናገሩት፡፡
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን የጭልጋ ነዋሪ የሆኑት የአይን እማኝ እንደገለፁት ደግሞ በከተማዋ ከጥር 24/2011 ዓ ም ጀምሮ በከተማዋና አካባቢዋ አለመረጋጋት መኖሩን ጠቁመው ዛሬ አንፃራዊ ሰላም አለ ነው ያሉት፡፡ ሆኖም በከተማዋ ከባንኮች በስተቀር ሌሎች የመንግስት መስሪያ ቤቶች ለአገልግሎት ክፍት አይደሉም ብለዋል፡፡
የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ፖሊስ መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር እንየው ዘውዴ በበኩላቸው ችግሩ የሁለቱም ዞኖች የተለያዩ አካባቢዎች አሁንም መቀጠሉን፣ በህይወትና ንብረት ላይ ቁጥሩና መጠኑ የማይታወቅ ጉዳት መድረሱን አመልክተዋል፡፡
ባለፈው ወርም በመተማ አካባቢ ኮኪት በተባለ ቦታ ላይ በህብረተሰቡና በፀጥታ ኃይሉ መካከል በተፈጠረ ግጭት የሰው ህይዎት መጥፋቱ የሚታወስ ነው፡፡
አለምነው መኮንን
ኂሩት መለሰ