1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ደቡብ ሱዳን፤ ተስፋና ቀቢፀ ተስፋ

ዓርብ፣ ጥር 13 2008

ለአዲሱቱ አፍሪቃዊት ሐገር ፖለቲከኞች እንግዳ አይደለም። እየተደራደሩ ይዋጋሉ። እየተስማሙ ይፋረሳሉ። እየተወያዩ ይጣላሉ። ሁለት ዓመት ከሁለት ወር። የአራት-ዓመት ከመንፈቁ የነፃነት ታሪኳም መሳለመሳ ነዉ። የሠላምና-የጦርነት

https://p.dw.com/p/1HiTf
ምስል Yohannes G/Eziabhare

[No title]

የደቡብ ሱዳን ተፋላሚ ሐይላት ከዚሕ ቀደም በተፈራረሙት ሥምምነት መሠረት ዛሬ ብሔራዊ የአንድነት መንግሥት መመሠረት ነበረባቸዉ። ይሁንና ሥለሚመሠረተዉ መንግሥት እስከ ትናንት ድረስ ጁባ ዉስጥ ሲደራደሩ የነበሩት የመንግሥትና የአማፂዉ ቡድን ተወካዮች ዛሬ መንግሥት ለመመሥረት አልተግባቡም።ሁለቱ ወገኖች መንግሥት የሚመሠረትበትን ጊዜ ላለማክበራቸዉ እርስበርስ እየተወቃቀሱ ነዉ።ከፕሬዝደንት ሳልቫ ኪር መንግሥት ባለሥልጣናት ጋር ለሚደራደሩት ለአማፂዉ ቡድን ተወካዮች የመጓጓዢያ፤ የሆቴልና የቀልብ ወጪን የሚሸፍኑት ምዕራባዉያን መንግሥታት ከዛሬ ጀምሮ ክፍያዉን እንደሚያቋርጡ አስታዉቀዋል።ጄምስ ሺማንዩላ የዘገበዉን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።

ግራ አጋቢ ነዉ።ግን ለአዲሱቱ አፍሪቃዊት ሐገር ፖለቲከኞች እንግዳ አይደለም።እየተደራደሩ ይዋጋሉ።እየተስማሙ ይፋረሳሉ።እየተወያዩ ይጣላሉ።ሁለት ዓመት ከሁለት ወር።የአራት-ዓመት ከመንፈቁ የነፃነት ታሪኳም መሳለመሳ ነዉ።የሠላምና-የጦርነት።ለዛሬ በተያዘዉ ቀጠሮ ለሠላሳ ወራት ይፀናል የተባለዉ የብሔራዊ የአንድነት መንግሥት ተመሠርቶ ቢሆን ኖሮ ይሕን የሠላም-የጦርነት መሳ ታሪክ ይቀይራል ነበር ተስፋዉ።

ሌላም ተስፋ ነበር። ጄኔራል ሳልቫ ኪር እና ያሁኑ ቀንደኛ ጠላታቸዉ ዶክተር ሪክ ማቸር እንደ ቅድመ-ሁለት ዓመቱ ፕሬዝደንት እና ምክትል ሆነዉ ግራ-ቀኝ ተቀምጠዉ ለ12 ሚሊዮን ሕዝባቸዉ የሚታዩበት አጋጣሚ ነበር።

QUALITÄT Südsudan Kindersoldaten
ምስል DW/Degen

ሰወስተኛ ተስፋ ነበር።ከኪር ወገን 16፤ ከማቸር አስር፤ ታስረዉ ከተለቀቁት ሁለት፤ ከትናንሽ ፓርቲዎች ሁለት፤ ድምር ሰላሳ- ሚኒስትሮች ይሾማሉ-ነበር።አማፂያኑ ጁባ ሲገቡ ሕዝቡ በክብር እንዲቀበላቸዉ ፕሬዝደንት ሳልቫ ኪር ያደረጉት ጥሪም ተስፋ፤ ደስታዉን የሚያጠናክር ነበር።

«ወንድሞቻችሁ፤ እሕቶቻችሁ እና ልጆቻችሁ ወደ ሐገራቸዉ ወደ ደቡብ ሱዳን ሲመለሱ በደስታ እንድተቀሏቸዉ እጠይቃለሁ።በቅን ልቡና፤ በእርቀ-ሠላም እና በይቅርታ መንፈስ ተቀበሏቸዉ።ያለፈዉን ርሱት።አዲስ ገፅ ክፈቱ፤ አንዳችሁ በሌላችሁ ላይ መተማመንን አሳድሩ እና በሠላም እና በመፈቃቀር ኑሩ።»

ሁሉም ቢያንስ ለዛሬ ነበር ነዉ።የመንግሥት መመሥረቻዉ ቀጠሮ ያለመከበሩ ምክንያትም እንደ ደቡብ ሱዳን ታሪክ ግራ አጋቢ ነዉ።መንግሥት እንደሚለዉ የአማፂዉ ቡድን ተደራዳሪዎች ከጁባ ፓጋካ ወደሚገኘዉ ዋና ሠፈራቸዉ እንዲመለሱ መሪያቸዉ ሪክ ማቸር ጠርተዋቸዋል። የማቸር ወገኖች ደግሞ የመንግሥት ተወካዮች ጫና እያሳደሩ ነዉ ባዮች ናቸዉ።

ብሔራዊ የአንድነት መንግሥቱ በተያዘለት ቀን-ዛሬ ባለመመሥረቱ የተናደዱት የዩናይትድ ስቴትስና የአዉሮጳ ሕብረት ባለሥልጣናት በጁባዉ ድርድር የሚካፈሉትን የአማፂ ተወካዮች የመጓጓዢያ፤ የመኝታና የቀለብ ወጪን አንከፍልም ብለዋል።የኪር መንግሥት አስሮ የፈታቸዉ የገዢዉ የSPLM ፓርቲ የቀድሞ ዋና ፀሐፊ ፓጋን አሙም ግን ተስፋ አላቸዉ።

«ተስፋ አለኝ፤ ሠላም ብዙ ሰዎች ከጠበቁት ጊዜ ቀድሞ ይሰፍናል።ፈትሕ እንዲፀና በተለይ ሰለቦች ፍትሕ እንዲያገኙ ተጠያቂነትና ፍትሕ መኖር አለበት።የተጠያቂነትና የፍትሕ መኖር የሐገሪቱን (ቁስል) እንዲሽርም ያስችላል።ተጠያቂነት መኖሩ አስፈላጊ ነዉ።ምክንያቱም ደቡብ ሱዳን እስካሁን ያየቻቸዉን እንደ ጭፍጨፋ እና ዘር ማጥፋት የመሳሰሉ ከፍተኛ ጥፋቶች እንዳይደገሙ ለመከላከል ይረዳልና።»

Afrika Bildergalerie Kindersoldaten im Süd-Sudan
ምስል DW/A. Stahl

የፖለቲካ ተንታኝ አብረሐም አዎሌች ደግሞ የደቡብ ሱዳን ፖለቲከኞች አሁን ባይስማሙ እንኳ ከለየለት ጦርነት አይገቡም ይላሉ።

«እዚሕም እዚያም መቆራቆስ ይኖር ይሆናል።እንዚሕ ቶሎ ይቆማሉ ብዬ አላስብም።ይሕ ማለት ግን እስካሁን እንደነበረዉ ሙሉ ጦርነት ይከፈታል ማለት አይደለም።ያም ሆኖ ግጭቶቹ ከሰፉና ከተደጋገሙ ተፋላሚ ሐይላት ሥምምነታቸዉን አፍርሰዉ ወታደራዊ የበላይነት ለማግኘት መዋጋቸዉ አይቀርም።»

እና ጦርነትም-ሠላምም የለምም። ደቡብ ሱዳን።

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሠ