1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዶ/ር ነጋሶ ለኦሮሞ ህዝብ ትግል ያበረከቱት አስተዋጽኦ

ሰኞ፣ ሚያዝያ 21 2011

የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ለግማሽ ምእተ አመት በዘለቀው የፖለቲካ ተሳትፏቸው ውስጥ በተለይም የኦሮሞ ህዝብ ራሱን በራሱ እንዲያስተዳድር ፍትሃዊ ተጠቃሚነቱ እንዲረጋገጥ፣ ሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብቱ እንዲከበርለት መስራታቸውን ዶይቼ ቬለ (DW) ያነጋገራቸው የፖለቲካ ሰዎች እና ምሁራን ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/3Hf4U
Negasso Gidada ehemaliger Präsident von Äthiopien
ምስል DW/Y. Gebregziabher

ዶ/ር ነጋሶ ለኦሮሞ ህዝብ ትግል ያበረከቱት አስተዋጽኦ

ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ምሁራዊ አቅማቸውን ተጠቅመው የኦሮሞ ህዝብ ታሪክ እንዲታወቅ የራሳቸውን አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን የሚናገሩት አስተያየት ሰጪዎቹ ህዝቡ ባህሉ፣ ቋንቋው እና ማንነቱ እንዲከበር መታገላቸውን ያነሳሉ። “የኦሮሞ ህዝብ ተበድሏል፤ ተገፍቷል” የሚል የትግል መነሻ እንደነበራቸው የሚነገርላቸው የቀድሞው ፕሬዝዳንት በመንግስትም ሆነ በተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ ጎራ ተሰልፈው በነበረ ወቅት የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄን ይዘው መጓዛቸውን በቅርበት የሚያውቋቸው ያስረዳሉ። የኦሮሞ ህዝብን መብት ለማስከበር በኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ውስጥ ሆነው የታገሉት ዶ/ር ነጋሶ ኢህአዴግን ከተቀላቀሉ በኋላ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ጭምር ለብሄርተኝነት መታገል እንደሚቻል በተግባር ያስመሰከሩ መሆናቸውን ፕሮፌሰር ህዝቄል ጋቢሳ ይናገራሉ።

ዶ/ር ነጋሶ ከመንግስት ስልጣን ራሳቸውን ካገለሉ በኋላ ለቀድሞ ፕሬዝዳንቶች የሚሰጡ ጥቅማ ጥቅሞችን ለማግኘት በሚል ስለመብት መታገላቸውን ትተው በዝምታ መቀመጥን አልመረጡም። ዶ/ር ነጋሶ ትግላቸውን ቀጥለው በግል ተመራጭነት የህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤትን መቀላቀላቸው የትግላቸው ሰፊነት ማመላከቻ መሆኑን DW ያነጋገራቸው ፖለቲከኞች እና ምሁራን አብራርተዋል፡፡

ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ። 

ሰለሞን ሙጬ

ተስፋለም ወልደየስ 

እሸቴ በቀለ