1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዶክተር ደብሩ ጉባ አዲሴ

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 17 2013

ዶ/ር ደብሩ ከ10 ዓመት ወዲህ እውቃታቸውን ወደ ሃገራቸው የሚያሻግሩበትን ድልድይ ዘርግተዋል።ከማሕፀን ሐኪሟ ጀርመናዊት ባለቤታቸው ጋር በጀመሩት ፕሮጀክት በኢትዮጵያ የተለያዩ ከተሞች በሚገኙ ሆስፒታሎች የሚሰሩ የማሕፀን ሐኪሞች ጀርመን መጥተው በዘርፉ ከፍተኛ ትምሕርት እንዲቀስሙ አድርገዋል።ባለፉት10 ዓመታት 120 ሐኪሞች በዚህ እድል ተጠቅመዋል።

https://p.dw.com/p/3kVw2
Äthiopien Operationssaal; Debru Guba Adisse
ምስል Debru Guba Adisse

ዶክተር ደብሩ ጉባ አዲሴ

በህክምና ሞያ ከተሰማሩ 35 ዓመት ሆኗቸዋል።ከዚህ ውስጥ ብዙ ዓመታት የሰሩት ከፍተኛ የሕክምና ትምሕርታቸውን በተከታተሉባት በጀርመን ነው። ሥራቸውና ኑሮአቸው ጀርመን ቢሆንም ያደጉባትንና ሕክምና የተማሩባትን የትውልድ ሃገራቸውን ኢትዮጵያን በሙያቸው ከማገዝ ቦዝነው አያውቁም። ከላይፕሲሽ ጀርመን ወጣ ብሎ በሚገኘው አይልንቡርግ በተባለው ከተማ ውስጥ ባለ ሆስፒታል አሁን ከፍተኛ ሐኪምና አማካሪ ናቸው።በሆስፒታሉ ለ26 ዓመታት በተለያዩ ደረጃዎች አገልግለዋል።ከዚያ በፊት ለስፔሻላዜሽን በመጡበት በበርሊን ለሦስት ዓመታት ሰርተዋል።ወደ ጀርመን ከመምጣታቸው በፊት በጅጅጋ ዩኒቨርስቲም በሃላፊነት ሰርተዋል።እዚያ ሳሉ በኮሌራ ላይ ባካሄዱት ምርምር ተሸልመዋል።የማሕፀን ሐኪም ዶክተር ደብሩ ጉባ አዲሴ የጎንደር የሕክምና ሳይንስ ኮሌጅ ካስመረቃቸው የመጀመሪያዎቹ የህክምና ተማሪዎች አንዱ ናቸው። 
። የተወለዱት ጭሮ አሰበተፈሪ አርበረከቴ በተባለች የገጠር ከተማ ነው።የ5 ስድስት ዓመት ልጅ ሳሉ አባታቸው ከዚህ ዓለም በአደጋ በሞት ሲለዩ ባህርዳር ይሰሩ የነበሩት አጎታቸው አቶ ፍስሀ ሲሳይ የእህታቸውን ሸክም ለማቅለል የደቡሩን እናትና ደብሩን ጨምሮ ሁለት ልጆቻቸውን ወስደው ማስተማር ጀመሩ።አንድ ዓመት ከቆዩ በኋላ አጎታቸው ወደ አዲስ አበባ ሲዛወሩ በአዲስ አበባ የመጀመሪያ ደረጃ ትምሕርታቸውን የቀጠሉት ህጻን ደብሩ አጎታቸው ለትምሕርት ከኢትዮጵያ ውጭ ሲሄዱ ደግሞ እናታቸው ጭሮ ተመልሰው ነበርና እስከ አስረኛ ክፍል እዚያው ተምረዋል።አጎታቸው ወደ ኢትዮጵያ ሲመለሱ 11ኛ እና 12ተኛ ክፍልን በአዲስ አበባ ሽመልስ ሃብቴ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርት ቤት ካጠናቀቁ በኋላ ነበር ጥሩ ውጤት አምጥተው ጎንደር ህክምና ለማጥናት የበቁት።ተመርቀው ጅጅጋ ሦስት ዓመት እንደሰሩ የትምሕርት እድል አግኝተው የዛሬ 32 ዓመት  በርሊን ጀርመን መጡ።የማህፀን ሕክምና እያጠኑ ትዳር መስርተው ኑሮአቸውን ጀርመን አደረጉ። ዶክተር ደብሩ እንደሚሉት በመሆናቸው ከህብረተሰቡ ጋር ለመዋሃድ ብዙም ጊዜ  አልወሰደባቸውም።

Äthiopien Operationssaal; Debru Guba Adisse
ምስል Debru Guba Adisse
Äthiopien Operationssaal; Debru Guba Adisse
ምስል Debru Guba Adisse


ዶክተር ደብሩ በስራ ባልደረቦቻቸው ዘንድ ተወዳጅና ተናፋቂ መሆናቸውን ይናገራሉ። በጀርመን ቆይታቸው ራስን ለማሳደግ በሚደረግ ጥረት በተለይ ብዙ ዓመታት እንግሊዘኛ ተምሮ ለመጣ እንደርሳቸው ላለ ሰው ቋንቋ ፈታኝ መሆኑን ያስረዳሉ።በስራው ዓለም እንደ ውጭ ዜጋ ሌሎች ተግዳሮቶችም  መኖራቸው አይቀረም። በዶክተር ደብሩ መርህ ደካማ ጎንን አሸንፎ ራስን ከሌላው ጋር ማስተካከል ቢቻል በልጦ መገኘት የውጭ ዜጎችን ለችግር የሚዳርጉ ቀደዳዎችን መድፈኛ ዘዴ ነው።ዶክተር ደብሩ አስር ዓመት ወዲህ እውቃታቸውን ወደ ሃገራቸው የሚያሻግሩበትን ድልድይ ዘርግተዋል።የማሕፀን ሐኪም ከሆኑት ጀርመናዊት ባለቤታቸው ጋር በጀመሩት ፕሮጀክት በኢትዮጵያ  የተለያዩ ከተሞች በሚገኙ ሆስፒታሎች የሚሰሩ የማሕፀን ሐኪሞች ጀርመን መጥተው በዘርፉ ከፍተኛ ባለሞያ መሆን የሚያስችላቸውን ትምሕርት እንዲቀስሙ አድርገዋል።ባለፉት አስር ዓመታት 120 ሐኪሞች የዚህ እድል ተጠቃሚ ሆነዋል።ፕሮጀክታቸው የጀርመን የማህጸን ሐኪሞች ማኅበርንና የነጻ ትምሕርት እድል የሚሰጠው የጀርመን የአካዳሚ ትምሕርት ልውውጥ አገልግሎት ድጋፍ አለው።ዶክተር ደብሩና ባለቤታቸው በግላቸውና ከሌሎችም ለጋሾች ጋር በመሆን በልዩ ልዩ እርዳታዎች ላይ ይሳተፋሉ።ከመካከላቸው በኢትዮጵያ የኮሮና ወረርሽኝ እንደገባ ለህክምናው የሚያገለግሉ መሳሪያዎችን አሰባስቦ በመላክ ያደረጉት አስተዋጽኦ ይገኝበታል።

ኂሩት መለሰ