1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ጀርመናዉያን ሙዚቀኞች በአዲስ አበባ «አንድነን»

ሐሙስ፣ ሰኔ 23 2008

« ሙዚቃ የዓለምን ሕዝብ አንድ ያደረገ፤ እያደረገም ያለ ነዉ። ሙዚቃ ያግባባናል። አንድ ሰዉ ከሌላ ሃገር መጥቶ ከኔ ጋር መሥራት ሲፈልግ በመሃል እያገናኘ ያለዉ ሙዚቃ ነዉ። የቆዳ ቀለማችንም ተለየ ጀርመናዊም ሆነ፤ ኢትዮጵያዊም ሆነ ሌላ አፍሪቃዊ አንድ ነን ብዬ አምናለሁ። ዋናዉ ነገር ሰዉን አንድ የሚያደርገዉ አስተሳሰቡ ነዉ።»

https://p.dw.com/p/1JGnk
Äthiopien Viva con Aqua Auftritt Clueso und Samuel Yirga in Addis Abeba
ምስል Christoph Köstlin für Viva con Agua

ጀርመናዉያን ሙዚቀኞች በአዲስ አበባ «አንድነን»

ጀርመናዉዊና ኢትዮጵያዊ ሙዚቀኞች በአንድ መድረክ ቀርበዉ ሁለቱም ከያኒኒያን የየሃገራቸዉን ባህላዊ ሙዚቃን በጋራ አንድ ሙዚቃን አቀናብረዉ በአንድ መድረክ ሲቀርቡ ምን አይነት ሙዚቃን ሊያስደምጡ እንደሚችሉ ይገምታሉ? ኢትዮጵያዊዉ ሙዚቀኛ «አንድ ነን» ይላል ሙዚቃ የዓለም ሕዝብ የመነጋገርያ ዋንኛና ቀዳሚ ቋንቋ በመሆኑ። በዛሬዉ ዝግጅታችን አንድ ጀርመናዊ የፖፕ ሙዚቃ ተጫዋቾችንና አንድ ታዋቂ ኢትዮጵያዊ የፒያኖ ተጫዋችን በአንድ መድረክ አዲስ አበባ፤ ያዘጋጁትን የሙዚቃ ቅንብርና ዓላማዉን እንቃኛለን።

ኩሉዞ በሚልየመድረክ ስሙ የሚታወቀዉ ጀርመናዊዉ የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝ ቶማስ ሁብነር፤ እንዲሁም ማክስ ሄረ ከታዋቂዉ ኢትዮጵዊ ወጣት የፒያኖ ተጫዋች ከሳሙኤል ይርጋ ጋር በጋራ አዲስ አበባ ሙዚቃ ካቀረቡ በኋላ፤ የዶይቼ ቬለዉ የጀርመንኛ ቋንቋ የባህል መሰናዶ፤ ሰሞኑን ይዞ በቀረበዉ ዘገባዉ የጀርመን የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝ ከኢትዮጵያዊዉ የፒያኖ ተጫዋች ጋራ በጋራ ፤ አንድ ነን በሚል ርዕስ ሰፋ ያለ ዘገባን አስነብቦአል።

ዘገባዉ ሲጀምር፤ በአንድ ክፍል ዉስጥ የቆመዉን ፒያኖ እየመታ ክፍሉን ዉብ በሆነ ሙዚቃ ሞልቶታል ሳሙኤል ይርጋ፤ ኩሉዞ በሚል የመድረክ ስሙ የሚታወቀዉ ጀርመናዊዉ ሙዚቀኛ ቶማስ ሁብነርና ማክስ ሄረ ተመስጠዉ ያዳምጣሉ። ኩሉዞ በተለይ እዚህ በጀርመን በሂፕ ሆፕ ጃዝ እና ፖፕ ሙዚቃዎቹ ተደናቂነትን አግኝተዋል። የ 36 ዓመቱ ጀርመናዊ ሙዚቀኛ ቶማስ ሁብነር በርካታ የዓለም ሃገራትን ጎብኝቶ አይቶአል። ኢትዮጵያን ሲጎበኝ ግን ይህ የአሁኑ ለመጀመርያ ጊዜ ነዉ። ወደ ኢትዮጵያ ለመሄድ የበቃዉም በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ለሚኖሩ አካባቢዎች ንጹሕ የመጠጥ ዉኃን የሚያቀርበዉን «ቪቫ ኮን አጉዋ» «Viva Con Agua» የተባለዉን ፕሮጀክት ለመጎብኘት ነበር። ሙዚቀኛዉ ኩሉዞ ኢትዮጵያን ለመጎብኘት የተነሳበት ዓላማ ንጹሕ የመጠጥ ዉኃን የሚያቀርበዉን «Viva Con Agua» ፕሮጀክትን ይሁን እንጂ በጉዞዉ ሙዚቃ መጫወት ንፁሕ የመጠጥ ዉኃ አቅራቢዉን ድርጅት ለመርዳት ሌላዉ የጉዞዉ ዓለማም ነበር። ታድያ መዲና አዲስ አበባ ላይ ወጣቱ የፕያኖ ተጫዋች ሳሙኤል ይርጋን። የኢትዮጵያ ሙዚቃ ይላል ኩሉዞ፤ በመቀጠል
«በጣም የተለየ የሙዚቃ አይነት ነዉ፤ የተለየ ቅላጼ,,, ለኔ ይህ በጣም አዲስ ነዉ። የምጫወተዉ የሂፕ ሆፕ ሙዚቃን ነዉ ፤ የሙዚቃ ደራሲም ነኝ ።»

የኩሉዞ የሞያ አጋር ማክስ ሂረም ኮሉዞ የሚናገረዉን እየሰማ ለአዎታ አንገቱን ይነቀንቃል። ማክስ በጀርመን ታዋቂ ሙዘቀኛና በተለይ በጀርመን ሂፕ ሆፕ ሙዚቃ ዘርፍ ተጠቃሽ የሆነ ሙዚቀኛ ነዉ። ለማክስ ሄረ ይህ የኢትዮጵያ ጉዞ የመጀመርያ አይደለም። ኢትዮጵያን እየተመላለሰ ጎብኝቶአል። እንዳዉም ከቅርብ ወራቶች በፊት በአዲስ የሚያሳትመዉን የሙዚቃ አልበም ፊልም በከፊል ኢትዮጵያ ዉስጥ ነዉ ያስቀረፀዉ። በጀርመንኛ ሙዚቃዉ በርግጥም የኢትዮጵያ ጃዝ ሙዚቃን እንዳካተተም ገልፆአል።

«ኢትዮ ጃዝ በምወደዉ የሙዚቃ ዘርፍ ብዙ ነገርን እንዳይ እንዳዉቅና እንድረዳ አድርጎኛል። ቅላጼዉ ጠንካሪ ያለዉ፤ አስደናቂ የጉጉትን ስሜትም ሆነ ትንሽ ሃዘን ትካዜን የሚያስጨብጥ ዓይነት ነዉ። ሙዚቃዉ መሳጭ ነዉ።»

ኢትዮ-ጃዝ ሙዚቃ ለየት ያለ የምዕራባዉያን የሙዚቃ ስልት እና የኢትዮጵያ ሙዚቃን ያካተተ ኢትዮጵያ የጃዝ ሙዚቃ አይነት ነዉ። በስድሳዎቹ ዓመታት የኢትዮ-ጃዝ ሙዚቃ አባት ተብሎ በሚታወቀዉ በሙዚቀኛ ሙላቱ አስታጥቄ ነዉ የተፈጠረዉ። ከዓመታት ወዲህ የኢትዮ-ሙዚቃ ስልት አንዲም በዛ ብሎ ሌላ ጊዜም አነስ ብሎ ቅላጼዉ ስልቱ ተለዋዉጦአል። የኢትዮጵያ የጃዝ የሙዚቃ ስልት በአንጋፋዉ ኢትዮጵያዊ ሙዚቀኛ ሙላቱ አስታጥቄ የዓለምን የሙዚቃ መድረክ ከረገጠ በኋላ ተወዳጅነቱ እየሰፋ መምጣቱ ይታወቃል። እንደ ባህል ሙዚቃችን ሁሉ መለያችንን የሆነዉ ኢትዮ-ጃዝ የዓለምን የሙዚቃ አፍቃሪዎች ይበልጥ እየማረከ መሆኑም ወደ ኢትዮጵያ እያሳበ መሆኑ ተነግሮለታል፤ በርካታ ጃዝ አፍቃሪ ኢትዮጵያዉያን ሙዚቀኞችም ብቅ ብቅ እያሉ ነዉ። ጀርመናዉያኑንም እንደሰማችሁት ማርኮአል። ታዋቂዉ የፒያኖ ተጫዋች ሳሙኤል ይርጋ፤
« ከልጅነቴ ጀምሮ የተለያዩ ሙዚቃዎችን አዳምጣለሁ። የምቻወተዉን ብቻ ሳይሆን፤ የተለያዩ ሃገር ባህል ሙዚቃዎችን አዳምጣለሁ። አንድ ሙዚቀኛ የተለያዩ ሙዚቃዎችን ማድመጥ አለበት ብዬም አምናለሁ። ያንን በማድረጌ ከልጅነቴ ጀምሪ ፖፕ፤ ጃዝ፤ ሮክ፤ የአፍሪቃን ጃዝም፤ ኢትዮ ጃዝንም ሳዳምጥ ስለነበር፤ ከጀርመናዉያኑ ሙዚቀኞች ማክስና ኩሉዞ ጋር ሙዚቃን ለመስራት ይህ ሃሳብ ሲመጣ ብዙ የሚያግባቡን ነገሮች ነበሩ። እነማክስም በጣም ደስተኞች ነበሩ የነሱን ሙዚቃ በመረዳቴ። ኩሉዞ ከኔ ጋር ስንቻወት በጣም ፈጣን ነበር። ሙዚቃዎችን የመረዳት አቅሙ በጣም ፈጣን ነበር በጣም ተሰጦ ያለዉ ሙዚቀኛ ነዉ። እነሱም ከኔ ጋር በመስራታቸዉ ደስተኞች ነበሩ። አዲስ አበባ ላይ ጥሩ ጊዜን አሳልፈናል። »

የተለያየ ሙዚቃን ስለማደምጥ ለሙዚቃ ስራዎቼን እጅግ ያቀልልኛል ማክስና ኩሉዞ ጋርም ለመስራት ችግር አልገጠመኝም። ኩሉዞ ሙዚቃን ለማወቅ እና ለመማር በጣም ፈጣን ሆኖ አግንቸዋለሁ። ሁለቱ ጀርመናዉያንና እዉቁ ኢትዮጵያዊ የፒያኖ ተጫዋች ሳሙኤል ይርጋ ጋር በጋራ ወደ መድረክ ለመቅረብ ልምምድ ሲያደርጉ ነዉ ያመሹት። የሳሙኤል የሙዚቃ ባንድ አስር ሙዚቀኞችን ያካተተ እንደሆነም ተዘግቦአል። ጀርመናዊዉ ሙዚቀኛ ኩሉዞ በሳሙኤል ይርጋ የሙዚቃ ችሎታ በጣም መማረኩን ገልፆአል።

« ሳሙኤል ይርጋ የተለየና ግሩም የሆነ የሙዚቃ ችሎታ ያለዉ ጠንካራ ሰራተኛ ነዉ። ሳሙኤል ምን ያህል ታግሎና ጠንክሮ ሰርቶ ይህን ሙዚቃ መጫወት እንደቻለና ተቀባይነት እንዳገኘ ሰዎች የሱን ታሪክ የሚያዉቁ ይመስለኛል። እኔም ሁኔታ እረዳለሁ። ሙዚቃን ስጀምር እኔም ብዙ መሰናክሎች ገጥመዉኛል።»
ሳሙኤል ሙዚቀኛ ለመሆን ሲያቅድ ዓላማዉ ላይ ለመድረስ ብዙ ዉጣ ዉረዶችን እንዳለፈ ተተርኮአል። ሙዚቀኛ ልሆነዉ በማለቱ በመጀመርያ የገዛ ቤተሰቦቹ አልወደዱለትም ነበር። በሙዚቃ ሕይወቱን ይመራል የወደፊት ኑሮዉን ያስተካክላል የሚልም እምነት አልነበራቸዉም። ሙዚቀኛ ሳሙኤል ጥርሱን ነክሶ ተምሮ ታዋቂና ድንቅ ሙዚቀኛ ለመሆን የበቃ ገና በድንቅ ስራዉ መሰላሉን እየወጣ ያለ ትልቅ የሙዚቃ ብቃት ያለዉ ሲሉ ጀርመናዉያኑ መስክረዉለታል። የሰላሳ ዓመቱ ሳሙኤል ይርጋ በዓለም አቀፍ የሙዚቃ መድረክ ዉል ለማግኘት የታጨ መሆኑም የተመለከተዉ። ሙዚቀኛ ይርጋ በጀርመን የሙዚቃ መድረክ እጅግ ታዋቂ የሆኑትን ሙዚቀኞች አዲስ አበባ ላይ ሲያገኝኛ ለሙዚቃ በጋራ አንድ መድረግ ላይ ሊሰለፍ ሲዘጋጅ አንድ ሃሳብ አፈለቀ አንድ ነን አላቸዉ ዊ አር ዋን።

ጀርመናዉያኑና የፒያኖ ተቻዋቹ ሳሙኤል ይርጋ ያዘጋጁት የገቢ ማሰባሰብያ የሙዜቃ ድግስ እጅግ ማራኪ እንደነበር ተዘግቦአል። ይህንኑ ሙዚቃቸዉን አንድነን በሚል ስም በሙዚቃ አልብም በቅርቡ ለሙዚቃ አፍቃሪ ጆሮ እንደሚደርስ ተነግሮአል። ለሁለቱ የጀርመን ሙዚቀኞች የኢትዮጵያ ይህ ጉዞአቸዉ ስኬታማ እንደነበር፤ ተመልሰዉ ኢትዮጵያን መጎብኘታቸዉ አይቀሪ እንደሆነ ተዘግቦአል። በጉዞዉ ጥሩና ደስ የሚለዉ ነገር ተመልሼ በቅርቡ መምጣቴን ሳስበዉ ነዉ።
የጀርመናዉያኑና የኢትዮጵያዊዉ የጋራ መድረክ የሙዚቃ ድግስ አዲስ አበባ ላይ አላበቃም። ከ 12 /15 ቀናት በኋላ በሰሜናዊ ጀርመን የወደብ ከተማ በሆነችዉ ሃንቡርግ ላይ የጋራ የሙዚቃ ድግስ መድረኩ ይቀጥላል። ሙዚቀኛ ሳሙኤል ለዚሁ ድግስ ወደ ጀርመን መግብያ ቪዛ ሲጠይቅ በመጉላላቱ ማዘኑን ገልፆአል። የኋላ የኋላ ግን ወደ ጀርመን መግብያ ፈቃድ ቪዛን ማግኘቱንና ለበጎ ሥራ ሙዚቃን ሃንቡርግ ላይ ለመጫወት የሚችልበት ሁኔታ መፈጠሩ እንዳስደሰተዉ ሳይገልፅ አላለፈም።

Äthiopien Viva con Aqua Auftritt Clueso und Samuel Yirga in Addis Abeba
ምስል Christoph Köstlin für Viva con Agua
Äthiopien Viva con Aqua Auftritt Clueso und Max Herre in Addis Abeba
ምስል Christoph Köstlin für Viva con Agua


አዜብ ታደሰ


ነጋሽ መሐመድ