1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ፈትል የብሬል ጋዜጣ በኢትዮጵያ

ዓርብ፣ ጥቅምት 6 2013

ተፈጥሮ ምክንያት ሽታ ይሁን በኑሮ ዝግመት አንዳች እክል ቢገጥማቸው ፣ ከሰው የሥሜት ሕዋሳቶች አንዱ ዐይናቸው ቢጎድል ምናልባትም መንገድ ሲሻገሩ ፣ ከእንቅፋቱና መጋጋጡ አስበንላቸው እጃቸውን ይዘን መንገድ አሻግረናቸው ይሆናል።

https://p.dw.com/p/3k1WN
Äthiopien Addis Ababa | Braille-Zeitung | Feyori Tewolde
ምስል Solomon Muche/DW

የመጀመርያው ለዐይነ ሥውራን የተዘጋጀ ጋዜጣ


ተፈጥሮ ምክንያት ሽታ ይሁን በኑሮ ዝግመት አንዳች እክል ቢገጥማቸው ፣ ከሰው የሥሜት ሕዋሳቶች አንዱ ዐይናቸው ቢጎድል ምናልባትም መንገድ ሲሻገሩ ፣ ከእንቅፋቱና መጋጋጡ አስበንላቸው እጃቸውን ይዘን መንገድ አሻግረናቸው ይሆናል። አልያም በታዳጊዎች እየተመሩ ሲጓዙ እተመልክተን ያዘንን እንኖራለን። ማመልከቻም ደብዳቤም ፅፈንላቸው ይሆናል። ይልቁንም ጥቂት ቢሆኑም ልበ ብርሃን ሆነው ማየት እየቻለ ማስተዋል የጎደለውን የሚመሩ የዕውቀት ብርሃን ፈንጣቂዎች ሆነው ኖረው ያለፉ በታሪክ ይህ ነው የማይባል በጎ ተፅዕኖ ያተሙም ብዙ ናቸው። በኢትዮጵያ ለዐይነ ሥውራን ትምህርት ካለመስፋፋቱ በላይ በብሬል ማንበብን የተማሩትም ቢሆኑ ብዙ የሚነበብ ነገር አያገኙም። መጽሐፍት፣ ጋዜጦችንና መጽሔቶችንም እንደ ሌላው ብዙም አያገኙም። ይህንን ጉድለት የተመለከተች አንድ ወጣት ከአንድ ወር በፊት ጀምሮ ለንባብ የበቃችና  " ፈትል " የተባለች ለዐይነ ሥውራን ያምትሆን የብሬል ጋዜጣን ማሳተም ጀምራለች። የዚህ ሀሳብ አመንጪ እና ወደተግባር ቀያሪዋ ወጣት ፍዮሪ ተወልደ ትባላለች። "በማኅበረሰብ ውስጥ እንደመኖራችን ችግሮችን እናውቃለን፣ በተለይም አዲስ አበባ አራት ኪሎ አካባቢ ሰዎች በጋዜጣና መጽሔቶች መረጃ፣ የሥራ እና የጨረታ ማስታወቂያዎችን ያገኛሉ ነገር ግን ለዐይነ ሥውራን ይህ ምቹ ሁኔታ የለም። ስለሆነም ወደዚህ ስራ ለመግባት ምክንያት የሆነኝ አንዱ ይህ ነው "ብላለች።
ጋዜጣዋ ለመጀመርያ ጊዜ ታትማ ለንባብ የበቃችው መስከረም 6 ቀን 2013 ዓ.ም ነበር። እስካሁን አራት ዕትሞች ለዐይነ ሥውራኑ በውስን የስርጭት ሥፍራዎች እንዲዳረስ ተደርጓል። ሙሉ በሙሉ የእስካሁን ወጭውም በወጣቷ የግል ገንዘብ መሸፈኑን ተነግራለች። ጋዜጣዋ በይዘቷ እንደሌሎች መደበኛ ጋዜጦች ሁሉ ዜናዎችን፣ በአገር ውስጥም ይሁን በውጭ የሚታዩ ክስተቶችን ከመዘገብ ባሻገር ፣ ልዩ ልዩ ሀሳቦች የሚዳሰሱባቸው ዐምዶችንም ይዛለች ተብሏል።
ወጣቷ የጋዜጣዋ መስራች ብሬል ማንበብም ሆነ መፃፍ አትችልም። የዐይና ሥውራኑን ችግር ለመረዳትና መፍትሔ ይዞ ላማምጣትም የጉዳቱ ሰለባ መሆን ግድ አልሆነባህም። ፅሑፎችን ከተለያዩ ሰዎች እያሰባሰበች ፅሑፉ ወደ ብሬል ተቀይሮ በኢትዮጵያ ብሔራዊ የዐይነ ሥውራን ማኅበር በኩል በግሏ አሳትማ ታሰራጫለች።
በኢትዮጵያ ከ አራት ሚሊዮን በላይ ዐይነ ሥውራን እንዳሉ ይነገራል። ምን ያህሉ የብሬል ትምህርት እንዳገኙ ግን አይታወቅም። አሁን ላይ ይህ ጋዜጣ በአዲስ አባባ ውስን ሥፍራዎች ለአንባቢዎች እየቀረበ ነው። በቀጣይ ግን በመላ ሀገሪቱ እንዲሰራጭ ውጥን እንዳላት አዘጋጇ ተናግራለች። ትምህርት ቤቶች በየ ቤተ መጽሐፍቶቻቸው እየገዙ እንዲወስዱ እና የዐይነ ሥውራኑን ፍላጎት እንዲያሟሉ እንቅስቃሴ መጀመራንም እንዲሁ ገልፃለች።
" የመጀመርያው ለዐይነ ሥውራን የተዘጋጀ ጋዜጣ ስለሆነ በጣም ደስ ብሎናል። አካል ጉዳት ኖሮባቸው እያለ ነገር ግን ራሳቸውን አብቅተው እንዴት ትልቅ ደረጃ እንደደረሱ የትልልቅ ተምሳሌት ሰዎችንም ታሪክ የምናገኝበት በመሆኑ ይህ ለአካል ጉዳተኛው ጥንካሬ የሚሰጥ ነው" ሲሉ አንድ ጋዜጣውን እያነበቡ ያሉ ዐይነ ሥውር ሰው አስተያየታቸውን ገልፀዋል። ፈትል የብሬል ጋዜጣ በኢትዮጵያ በአይነቷ የመጀመርያ ሆና በታሪክ ተመዝግባለች።

Äthiopien Addis Ababa | Braille-Zeitung | Feyori Tewolde
ምስል Solomon Muche/DW
Äthiopien Addis Ababa | Braille-Zeitung | Feyori Tewolde
ምስል Solomon Muche/DW

ሰለሞን ሙጬ 
ሸዋዬ ለገሰ