ፎቶግራፍ እና ለውጥ-ከማኅደር ኃይለሥላሴ ጋር የተደረገ ቆይታ
ሐሙስ፣ ሰኔ 6 2011ለረዥም አመታት በፎቶ ቤቶች እና በውጭ አገር ዜጎች እጅ ተወስኖ የቆየው የፎቶግራፍ ሙያ ባለፉት አመታት በኢንተርኔት አገልግሎት እና ዘመናዊ ስልኮች መስፋፋት እየተለወጠ ይገኛል። ማኅደር ኃይለሥላሴ ይኸ ለውጥ ካፈራቸው የትውልዱ የፎቶ ባለሙያዎች መካከል አንዷ ነች። የምኅንድስና ትምህርት እና ሥራዋን በመተው በወደደችው የሥራ ዘርፍ የተሰማራችው ማኅደር ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ እና ኤኮኖሚያዊ ለውጦች በማኅበረሰብ ላይ የሚያሳድሩት ተፅዕኖ የሚዳስሱ ስራዎች አሏት። በኢትዮጵያ እና በውጭ አገራት ስራዎቿን ለዕይታ አቅርባለች።
ተወልዳ ያደገችው በአዲስ አበባ ነው። ማኅደር በፒያሳ፤ በመርካቶ፣ በእሪ በከንቱ፤ በአራት ኪሎ፤ በካዛንቺስ አዲስ አበባ የምታልፍባቸውን ለውጦች የሚያሳዩ ፎቶግራፎች አንስታለች። ማኅበራዊው፤ ኤኮኖሚያዊው እና ፖለቲካዊው ለውጥ የማኅደርን ትኩረት የሳበ በፎቶግራፍ የሚነገር ታሪክ ነው። ማስቲካ እና ሲጋራ ነጋዴው፤ ዘበኛ፤ ፈጫይ፤ የቀን ሰራተኛ፤ የጎዳና ተዳዳሪ ...ሁሉም በማኅደር ካሜራ የሚነገር ታሪክ አላቸው።
የ29 አመቷ ማኅደር ኃይለሥላሴ በኢትዮጵያ በፍጥነት በመስፋፋት ላይ በሚገኘው የፎቶግራፍ ሙያ ተቀባይነት ካገኙ ባለሙያዎች መካከል አንዷ ናት። በስራዋ እንደ ሴቶች፤ ሕፃናት እና እናቶች ያሉ ማኅበረሰቦችን የተመለከቱ ርዕሰ-ጉዳዮች ትኩረት ከምታደርግባቸው መካከል ይገኙበታል።
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምፅ ማዕቀፉን ይጫኑ!
እሸቴ በቀለ