1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ፔትሮናስ የነዳጅ ኩባንያ ከኦጋዴን እየወጣ ነው

ሐሙስ፣ ጥቅምት 4 2003

በኩባንያው የኢትዮዽያ ቅርንጫፍ በቅርቡ እንዳስታወቀው በኦጋዴን ክልል እያደረገ የቆየው ፍለጋ ውጤቱ እጅግ አነስተኛ በመሆኑ ይዞታዎቹን በመሽጥ ከኢትዮዽያ ይወጣል። የኢትዮዽያ ማዕድን ሚኒስቴር ጉዳዩ በሂደት ላይ በመሆኑ ፔትሮናስ ጠቅልሎ ወጥቷል ለማለት ጊዜው ገና ነው ይላል።

https://p.dw.com/p/Pe9X
የኦጋዴን ገጽታምስል dpa - Fotoreport

መሰረቱ ማሌዢያ ኩዋላላንፑር የሆነው ፔትሮናስ የነዳጅ ኩባንያ በጋምቤላና በኦጋዴን የነዳጅ ፍለጋ ለማከናወን ስራ የጀመረው ከሰባት ዓመት በፊት ነበር። ሳምንታዊው የአማርኛ ጋዜጣ ሪፖርተር እንደዘገበው ከሆነ ኩባንያው ለሰባት ዓመታት ያደረገውን የነዳጅ ፍለጋ አቋርጦ፤ ጓዙንም ጠቅልሎ እየወጣ ነው። በፔትሮናስ የኢትዮዽያ ጽ/ቤት 500 ሚሊዮን ዶላር በፈጀው የነዳጅ ፍለጋ ስራው መጠኑ አነስተኛ ከሆነ የነዳጅ ፍሰት በቀር ብዙም ውጤት እንዳላገኘ በሰጠው መግለጪያ አስታውቋል። ኩባንያው ሳውዝ ዌስት ኢነርጂ ለተሰኘ፤ ጽ/ቤቱን ሆንግ ኮንግ ላደረገ ኩባንያ ይዞታዎቹን ለመሸጥ መስማማቱም ተገልጿል። በማዕድን ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን የሥራ ሂደት ባለቤት አቶ ባጫ ፋጂ እንደሚሉት ፔትሮናስ ጠቅልሎ መውጣቱ ገና አለየለትም። ሂደት ላይ ነው ይላሉ።

ድምጽ

በእርግጥ በማዕድን ሚኒስቴር ጉዳዩ ገና አላለቀም። ከፔትሮናስ ጋር የተፈረመው ውል እንዳለ ነው። ሆኖም ፔትሮናስ ከሳውዝ ዌስት ኢነርጂ ጋር ያደረገው ስምምነት ተጠናቋል። ፔትሮናስ በኢትዮዽያ ያደረገውን ፍለጋ አቋርጦ የመውጣቱ ምክንያት በኩባንያው ባለሙያዎች እንደተገለጸው ኦጋዴን ውስጥ ሂላላ አከባቢ የተቆፈረው ጉድጓድ ውጤት አልባ በመሆኑ 2500 ሜትር ጥልቀት የደረሰው ቁፋሮ እንዲቋረጥ ተደርጓል። አቶ ባጫ ፋጂ ግን ኩባንያው ነዳጅ አጥቶ ነው የሚወጣው የሚለው ድምዳሜ ስህተት ነው፤ ገና አፈሩ እየተመረመረ ነው ይላሉ።

ድምጽ

በሌላ በኩል የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጪ ግንባር ፔትሮናስ ከኦጋዴን ለቆ የሚወጣው በክልሉ ባለው የጸጥታ ችግር እንደሆነ አስታውቋል። የግንባሩ የኢትዮዽያ ጉዳይ ሃላፊ አቶ ሀሰን አብዱላሂ፤ ፔትሮናስ በኦጋዴን ያለው ጸጥታ አስግቶት ነው የሚወጣው ይላሉ።

ድምጽ

በማዕድን ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን የሥራ ሂደት ባለቤት አቶ ባጫ ፋጂ፤ በጸጥታ ችግር መባሉን አይቀበሉም።

ድምጽ

ፔትሮናስን ተክቶ በኦጋዴን በነዳጅ ፍለጋ ላይ የሚሰማራው ሳውዝ ዌስት ኢነርጂ ዋና ጽ/ቤቱ ሆንግ ኮንግ ነው። አቶ ቴዎድሮስ አሸናፊ በተባሉ ባለሀብት እ.ኤ.አ.በ2005 እንደተቋቋመ ይነገራል። የትግራይ መልሶ ማቋቋም ድርጅት ንብረት ነው የሚሉ መረጃዎች ከአንዳንድ ወገኖች ይሰማል። አቶ ባጫ ፋጂ ግን ስለዚህ ጉዳይ የማውቀው የለም፤ ኢትዮዽያዊ ድርጅት መሆኑን አውቃለሁ ይላሉ።

ድምጽ

የሆኖ ሆኖ ፔትሮናስ የነዳጅ ኩባንያ የኦጋዴን ቆይታው ወደማብቃቱ ተቃርቧል። መሰረቱን ሆንግ ኮንግ ያደረገው ኢትዮዽያዊ ኩባንያ ሳውዝ ዌስት ኢነርጂ ሥራውን ተረክቦ ነዳጅ ለመፈለግ 200 ሚሊዮን ዶላር መድቧል።

መሳይ መኮንን

ተክሌ የኋላ