1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

28ተኛዉ የቩልዝቡርግ አፍሪቃ ፊስቲቫል

ሐሙስ፣ ሰኔ 9 2008

በጀርመን በጎርጎረሳዉ 1989 ዓ,ም ቩልዝቡርግ ከተማ የጀመረዉና ከአዉሮጳ እጅግ ግዙፍ እንደሆነ የሚነገርለት የአፍሪቃ ፊስቲቫል ዘንድሮ ከ80 ሺህ ታዳሚዎችን አሰባስቦ ነበር። ከሁለት ሳምንት ግድም በፊት ለአራት ቀናት የተካሄደዉ ይህ ፊስቲቫል ከአፍሪቃ የተለያዩ ሃገራት የተሰባሰቡ 250 ሙዚቀኞች ተሳፊ ነበሩ።

https://p.dw.com/p/1J7Gr
Würzburg Africa Festival Olivier Tshimanga Gitarrist und Sänger
ምስል DW/A. Gensbittel


ይህ መድረክ የአፍሪቃን ልዩ ልዩ አይነት ሙዚቃ፤ የአለባበስ፤ የአመጋገብ ባህልን የሚያስተዋዉቅበት አዉደ ርዕይም አለዉ። በየዓመቱ ከ 56ቱ የአፍሪቃ ሃገራትና ከካሪቢያን ስለሚሰባሰቡበት ስለ ቩልዝቡርጉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል የዶቼ ቬለዋ አዉደ ጌንዝ ቢትል የዘገበችዉን አሰባስበን ቀርበናል።
ወደ 80 ሺህ ጎብኝዎች የነበሩትና ከሁለት ሳምንት በፊት በጀርመን የተካሄደዉ ግዙፉ የቩልዝቡርግ ከተማ የአፍሪቃ ፊስቲቫል የአፍሪቃ ሙዚቃን፤ የአለባበስ፤ የአመጋገብ እንዲሁም የትረካ ባህሎችን ሁሉ ያቀረበበት መድረክ ነበር። ከኮንጎ የመጣዉ ባሊጋትር ከያኒ ኦሊቨር ትሽማንጋ ነበር። ይህን በአዉሮጳ ግዙፍ የተባለዉንና ለ 28 ኛ ጊዜ የተካሄደዉን የአፍሪቃ ፊስቲቫል በይፋ የከፈተዉ። በዚሁ የአራት ቀናት ፊስቲቫል ላይ ታዋቂዉ የኮት ዲቯር የሪጌ ሙዚቃ ኮከብ፤ በሂፕሆፕ ሙዚቃዋ የምትታወቀዉ የጀርመን ናይጀርያ ክልስዋ ሙዚቀኛ፤ እንዲሁም የደቡብ አፍሪቃዉ ታዋቂ የጃዝ ሙዚቃ አቀንቃኝ በዚሁ ፊስቲቫል ላይ ታድመዋል።
በአዉሮጳ ግዙፍ በተባለዉ በዚህ በቩልዝቡርጉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ በርካታ ታዋቂ የአፍሪቃ ከያንያን ሙዚቃዎቻቸዉን ለማሳየት በየዓመቱ ይመጣሉ። ይህ መድረክ በየአገራቸዉ ታዋቂ ኮከብ የሆኑ የአፍሪቃ ሙዚቀኞች አዉሮጳ እንዲተዋወቃቸዉ መንገድ የሚከፍት ከመሆኑም በላይ ሌሎች የመድረክ ላይ ዝግጅቶችን የሚያቀናብሩ የሙዚቃ ሰዎችን ሌሎች ሃገራት ሙዚቀኞችን የሚተዋወቁበት መድረክም ጭምር ነዉ። በርካታ የአፍሪቃ ታዋቂ ኮከብ ሙዚቀኞች ይህንን በየዓመቱ በቩልዝቡርግ ጀርመን በሚካሄደዉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ ከ 10 እና 15 ጊዜ በላይ መገኘታቸዉን ከዲሞክራቲክ ኮንጎ የመጣዉ ታዋቂ የጊታር ተጫዋች ኦሊቨር ትሽማንጋ ይናገራል። ወጣቱ የኮንጎ ታዋቂ ሙዚቀኛ በቅርቡ በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት የተለየዉ የኮንጎ ሙዚቀኛ ፓፓ ዊንባ የሙዚቃ ድግስ ላይ ጊታር በመጫወቱ ነበር፤ በአገሩ እዉቅን፤ ዝናን ያተረፈዉ። ኦሊቨር የጊታሩን እያገላበጠ የሚጫወትበትን ጥበብ የሙዚቃ ትዕይንት «ቲሽማንጎሎጊ» ሲል ሰይሞታል።

«ቲሽማንጎሎጊ» አንድ የሙዚቃ የአቀራረብ ስልት፤ ለየት ያለ የጊታር ጨዋታ አቀራረብ ስልት ነዉ። ሌላ አይነት የአቀራረብ ስልትን ለማስተዋወቅ በቅቻለሁ። በሙዚቃ ዉስጥም የሌላ የሙዚቃ አጨዋወት ስልት እንዲኖርበት አድርጌያለሁ። ሙዚቃዎቼ የፍላሚንጎ፤ የብሉዝ የፖፕ እንዲሁም የኮንጎ ሩምባ የሙዚቃ ስልት ቅይጥ ናቸዉ። ትንሽም የፈረንሳዩ ታዋቂ የጊታር ተጫዋች የ ያንጎ ራይንሃርድት የአጨዋወት ስልትም ይደመጥበታል። ስለዚህ ሙዚቃዎቼን ወጣት ሙዚቀኞች በመዉደዳቸዉና እኔን እንደአርዓያ በመዉሰዳቸዉ እጅግ እኮራለሁ»

ኮንጎዋዊዉ ታዋቂ የጊታር ተጫዋች ሙዚቃዎቹን የሚያስደምጠዉም ሆነ ልዩ የጊታር አጨዋወት ስልቱን የሚያሳየዉ ለሙዚቃ አፍቃሪዎቹ ወይም እሱን ለሚከተሉት ብቻ አይደለም። በሙዚቃዉ በማኅበራዊ ኑሮ ድጋፍ በሚስፈልግበት ሁሉ ድጋፍን ያደርጋል። ኮንጎዋዊዉ ታዋቂ ሙዚቀኛ በተለያዩ ጊዜያት ለጎዳና ተዳዳሪ ሕጻናት የገንዘብ ርዳታ ማሰባሰብያ የሙዚቃ ድግስን አዘጋጅቶአል። በኮንጎ መዲና ኪንሻሳ በሚገኝ አንድ ወላጆቻቸዉን ያጡ ሕጻናት ማዕከል ለሚገኙ ሕፃናትም የክርስትና አባት ነዉ። ኮንጎዋዊዉ ሙዚቀኛ ኦሊቨር ትሺማንጋ በአገሩ በብዙኃን መገናኛ በሚቀርብበትም ሆነ የሙዚቃ ድግሱ በሚያሳይበት ወቅት በምስራቅ ኮንጎ ዉስጥ ለምትገኘዉ ቢኒ ከተማ ፍቅር ሰላምና፤ ልባዊነት እንዲሰፍን መልክቱን ምክሩን ይለግሳል። በምስራቃዊ ኮንጎ ቢኒ፤ ከተማ በያዘነዉ የጎርጎረሳዉያኑ 2016 ዓ,ም ግንቦት ወር ዉስጥ፤ ዳግም የጅምላ ጭፍጨፋ ተከስቶአል። በቤኒና በሉብሮ የኮንጎ ምስራቃዊ ከተሞች፤ ከጎርጎረሳዉያኑ 2014 ዓ,ም ጀምሮ በቁጥር ከ 1000 የሚበልጡ ሰዎች በተለያዩ ታጣቂ ቡድኖች ተገድለዋል።
ከ80 ሺህ በላይ ታዳሚዎች በተገኙበት በጀርመንዋ የቩልስቡርግ ከተማ በሚደረገዉ ዓመታዊ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ሌላዉ ሙዚቀኛ ሎኩዋ ካንዛ ተገኝቶ ነበር። ካንዛ እንዲሁ ታዋቂ የዴሞክራቲክ ኮንጎ ሙዚቀኛ ነዉ። እንደ ካንዛ በምስራቅ ኮንጎ በተለያዩ ታጣቂ ቡድኖች ስለተገደሉት በርካታ ሰዎች ጉዳይ በጣም በጥቂቱ ነዉ የሚነገረዉ።

«ምንም ነገር መስራት የማይፈልጉትን፤ አባት፤ እናታችሁ፤ ልጅ እህታችሁ ያለምንም ክብርና ርህራሄ ልክ እንደ እንስሳ ሲገደሉ አስቡት እላቸዋለሁ። ስለዚህ ጉዳይ ማሰብማ መነጋገር ይኖርብናል። ምክንያም ሰዎች ሁሉ ትንሽ እንኳ ሰላም የማግኘት መብት አለን።» ዘንድሮ ለ 28ተኛ ጊዜ በጀርመን የቩልስቩርጉ በድምቀት የተከበረዉ ባህላዊ የሙዚቃ መድረክ ከአህጉሩ ከአፍሪቃ ራቅ ብሎ ወጥቶ ኪዩባን በክብር እንግድነት ጋብዞአል። የቩልስ ቡርጉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል አንዱ አዘጋጅ ኢቴኒ ኦፕል እንደተናገሩት ዘንድሮ ለምን የኪዩባ ሙዚቃና ኩባዉያን በክብር እንደተጋበዙ ሲገልፁ።

« ሙዚቃዉ፤ በቀድሞ ጊዜ በነበረዉ የቅኝ ግዛት ዘመንና ባርነት ዘመን አፍሪቃዉያን ወደ ኩባ ከመጋዛቸዉ ጋር ተያይዞ መምጣቱን ያሳያል። የቅን ግዛቱ ዘመን ምን አይነት ተጽዕኖ እንደነበረዉ ሙዚቃ በኅብረተሰቡ ላይ ያሳደረዉን አመለካከት፤ እንዲሁም ባህሉ ምን ያህል እንደተቀላቀለ የሙዚቃዉ ስር መሰረት፤ ከአፍሪቃ እንደመጣ የሚያሳይ ነዉ። ይህ ሁሉ በጣም አስደናቂና አጓጊ በመሆኑ ከዓመታት ጀምሮ ሙዚቃዉ አፍሪቃዊ መነሻ እንዳለዉ በርካታ መረጃ መኖሩን ለማግኘትና ለማሳየት እየሞከርን ነዉ። በኪዩባ ባህላዊ ሙዚቃ ዉስጥም ይህንን ነዉ የምናጤነዉ።»

ከጊኒቢሳዉ ወደዚሁ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ ለመካፈል የመጣችዉ ሙዚቀኛ ካርያና ጎሜዝ እንደምትለዉ ከሆነ ሙዚቃዎችዋ ዉስጥ ብዙ የኪዩባ ሙዚቃ ቅላጼ ይሰማል። ጎሜዝ ዘመናዊና ጥንታዊና ባህላዊ የሙዚቃ ቅላፄን በማቀላቀል ነዉ ሙዚቃዎችዋን የምታቀርበዉ። አባትዋ ጊኒ ቢሳዉ ከቅኝ ግዛት ለመላቀቅ ባደረገችዉ ትግል የረዱትን ቼኮቬራንና ፊደል ካስትሮን ሁሉ በግል እንደሚቃዉቋቸዉ፤ መኖርያ ቤት ድረስ ሁሉ ይመጡ እንደነበር ተናግራለች።

«ያደኩት በርካታ ኩባዉያን በሚኖሩበት አካባቢ ነዉ። እነዚህ ኩባዉያን የወላጆቼ ጓደኞች ስለነበሩ ወደ እኛ ቤት ሲመጡ ይጠዉ የሚመጡት የኩባ ሙዚቃን ነበር። ኪዩባ የጨረሰም አጎት አለኝ፤ ወደዚህ ሲመለስ ይዞ የመጣዉ የኪዩባን ሙዚቃ ነዉ። የኔን የሙዚቃ አልበም የሚደመጥጥ ሰዉ የኪዩባ ሙዚቃ ተፅኖ እንዳደረበት በደንብ ይረዳል። ቀደም ሲል በኪዮባ እና በጊኒቢሳዉ መካከል ትልቅ የወዳጅነት ግንኙነት ነበር »

በአፍሪቃ ሳለ ለየት ያለ የሙዚቃ ስልትን መጀመሩን የሚናገረዉ ሪጌማን በሚል መጠርያ የሚታወቀዉ ጀርመናዊዉ ሙዚቀኛ ያህኮስቲክስ ነዉ። የጀርመን ዴፕሎማት ልጅ ሆኖ በላይቤሪያ ግብፅ ኬንያን ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪቃ ሃገራት የኖረዉ ጀርመናዊዉ የሪጌ ሙዚቃ አቀንቃኝ በሜክሲኮ ዩኤስ አሜሪካ ኖርዋል።
«በዝያን ወቅት የ 12 የ 13 ዓመት እድሜ ልጅ እያለሁ ኬንያ ስኖር ነዉ የሪጌ ሙዚቃን ማድመጥ የጀመርኩት። እዝያ በመኖሪና ሌላ ባህልን በማየቴ የተለያዩ ሙዚቃን በማድመጤ ነዉ፤ በሙዚቃ ስራዬ ላይ ጠንካራ ተፅኖ ያሳደረበኝ። ይህ ሁሉ እኔ በምጫወተዉ ሙዚቃ ላይ ልዩነት ፈጥሮአል። ሰዎች ምን አይነት ሙዚቃ እንደምጫወት ያዉቃሉ። የምጫወተዉ ረቀቅ የሪጌ ሙዚቃን ነዉ።»

ይህንን የአፍሪቃ ፊስቲቫል ለማየት ከተለያዩ የጀርመን ከተሞች ወደ ቩልስቡርግ ይመጣሉ። በበርሊን ነዋሪ የሆኑት በየዓመቱ የቩልስቡርጉን የአፍሪቃ ፊስቲቫል ሊጎበኝ የሚመጣዉ ሰዉ ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ተናግረዋል። «ሙዚቃዉን እወዳለሁ፤ በየዓመቱ የቩልዝቡርጉን የሙዚቃ ፊስቲቫል የሚጎበኘዉ ሰዉ ቁጥር እጅግ እየተበራከተ ነዉ። በጣም ነዉ የተገረምኩት»

ሌላዉ የዚህ የአፍሪቃ ድግስ ታዳሚ የመጡት ደግሞ «የመጣሁት ከዴሞክራቲክ ኮንጎ ነዉ። የምማረዉ እዚህ ቩልዝቡርግ ዩንቨርስቲ ነዉ ። እዚህ በሚካሄደዉ በአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ በመገኘቴ በጣም ነዉ የተደሰትኩት። በአፍሪቃ አልፎ አልፎ የሚገኝ አጋጣሚን ነዉ እዚህ ለማየት የበቃሁት። በዚህ ፊስቲቫል አፍሪቃ ያለህ ያህል ይሰማሃል። አፍሪቃ በርግጥ ምን አይነት እንደሆነች ብዜ የተለያዩ ነገር መኖራቸዉንና ወቅታዊ የአፍሪቃ ርዕስን ሁሉ መስማትና ማየት ይቻላል። ለምሳሌ ዛሬ ስለ ስደተኛ ጉዳይ ዉይይት ነበር። በዚሁ ዉይይት ላይ አፍሪቃዉያን በመሳተፋቸዉ በጣም ነዉ የተደሰትኩት»

በሆላንድ ነዋሪ የሆነችዉ ኢትዮጵያዊትዋ ሙዚቀኛ ምንይሹ ክፍሌ ባለፈዉ ዓመት በቩልዝቡርጉ የአፍሪቃ ፊስቲቫል ላይ ቀርባ ነበር። ዘንድሮ ግን በሌሎች የጀርመን ከተሞች ሙዚቃዋን እንድታሳይ ተጋብዛ ስለነበር መገኘት አለመቻልዋን ነግራናለች። ሙዚቀኛ ምንይሹ የኢትዮጵያ ባህላዊ ዉዝዋዜና የምታሳይ የአማርኛ ሙዚቃን የምታስደምጥ የኢትዮጵያ አንባሳደር ሲሉ የተለያዩ የብዙኃን መገናኛዎች በተለያዩ ጊዜያት ዘግበዉላታል። ሙዚቃዎችም በፈረንጆቹ ጆሮ እንዲንቆረቆር ቀይጥ በማድረግ የተለያዩ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰብ ባህል ገላጭ ሙዚቃን ይዛ ነዉ ወደ መድረክ የምትቀርበዉ። በቅርቡ ይህንኑ ስራዋን ለጀርመን ሙዚቃ አፍቃሪዎችዋ አቅርባለች። ከሁለት ሳምንት በፊት በጀርመን ቩልዝቡርግ ከተማ በዓመታዊና ዘንድሮ ለ 28 ኛ ጊዜ ስለተካሄደዉ በአዉሮጳ የአፍሪቃ ግዙፍ ፊስቲቫል ያዘጋጀነዉን ሙሉዉን ቅብር የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን እንዲከታተሉ እንጋብዛለን።

አዜብ ታደሰ

Die Sängerin Minyeshu aus Äthiopien
ኢትዮጵያዊትዋ ሙዚቀኛ ምንይሹ ክፍሌምስል DW/A. Gensbittel
Africa Festival Würzburg 2013
ምስል picture-alliance/dpa
Soldaten der FARDC in der Nähe von Beni Kongo im Einsatz gegen Islamisten aus UgandaJanuar 2014
በምስራቅ ኮንጎ ዉስጥ ለምትገኘዉ ቢኒ ከተማ ነዋሪዎች በወታደሮች ጥበቃምስል Getty Images/AFP/Alain Wandimoyi
Würzburg Africa Festival Olivier Tshimanga Gitarrist und Sänger
ምስል DW/A. Gensbittel


ሸዋዬ ለገሠ