1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሕይወት የጠፋበት በሚድሮክ ኩባኒያ ዳግም የተነሳ ተቃዉሞ 

Merga Yonas Bula
ረቡዕ፣ ግንቦት 1 2010

የኢትዮጵያ ማዕድን ሚኒስቴር የሚዲሮክ ወርቅ ማእድን ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ የስራ ፍቃድ እድሳት ሰበብ ኩባንያው ወርቅ በሚያወጣበት በኦሮሚያ ክልል በጉጂ ዞን የተነሳው ተቃውሞ መቀጠሉን ነዋሪዎች ዛሬ ለዶቼቬለ ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/2xShH
Shakiso Town
ምስል Yidnekachew Gashaw

Protest Reignite on Midroc - MP3-Stereo

የማዕድን ኩባንያዉ በጉጅ ዞን በሻኪሶ ከተማ አቅራብያ ከሚገኘው ከለገ ዳምቢ ወርቅ ማውጫ የሚለቃቸዉ በካይ ኬምካሎች በሰዎችና በአከባቢው ተፈጥሮ ላይ ከፍተኛ ተፅእኖ አድርሰዋል በማለት ነዋሪዎች ተቃዋሞአቸውን ከትናንት አንስቶ ዳግም በማሰማት ላይ ናቸው። ባለፈዉ ቅዳሜ የቀድሞዉ የኢትዮጵያ የውሃ፣ የመስኖና የኤሌክትሪክ ሚኒስትር፤ አሁን የመከላክያ ሚኒስትር አቶ ሞቱማ ማቃሳ ኩባንያዉ ከ20 ዓመት በፊት 9  ስኩዌር ኪሎሜትር ስፋት ያለውም የማዕድን ቦታ በ192 ሚሊዮን ብር ሲገዛ ማዕድኑ በ20 ዓመት ዉስጥ ካላለቀ ዳግም ለ10ዓመት ፍቃዱ እንዲራዘምለት በተደረሰው ስምምነት መሰረት ፈቃዱ መታደሱን  ለጉጂ ዞን ማህበረሰቡ ማስረዳታቸዉን የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል። እንደ ዘገባዎቹ ከማዕድን ማውጪያው የሚለቀቀው ኬሚካል በሰዎች ጤናና በአካባቢ ላይ ጉዳት እንደማያደርስ ጥናት መደረጉን የጠቀሱት አቶ ሞቱማ ሆኖም በአከባቢ ላይ ጉዳት የሚያደርስ ከሆነ ግን ፍቃዱን በ10 ቀን ዉስጥ ማስቆም እንደሚቻል መናገራቸዉ ተጠቅሷል።

የአከባቢው ነዋሪዎች ከመንግስት መፍትሄ ስላላገኙ ከዚህ ሳምንት ሰኞ ጀምሮ የስራ፤ የትምህርትና የንግድ ማቆም አድማ ላይ መሆናቸውን እኝህ የአይን እማኝ ለዶይቼ ቬሌ ይናገራሉ።

በጉጅ ዞን በአዶላ ከተማ የሚገኘው የአዶላ ሆስፒታል ዋና ስራ አስከያጅ ዶክተር ጉሻ ባላኮ እስስካሁን ሆስፒታላችዉ የመጣውን አስከሬን እና ቁስለኛ ብዛት ተናግረዋል።

ዶክተር ጉሻ ባላኮ፤ «ሕይወታቸዉ ያለፈዉ አራት ሰዎች ናቸው፤ አስከሬናቸዉ ወደኛ ሆስፓታል የመጣዉ ማለት ነዉ። አምስት ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል። ከዚህ ዉስጥ ከባድ ጉዳት የደረሰባቸዉ ሶስት ሰዎች ወደ ሃዋሳ ሆስፒታል ተልከዋል። ቀሪዎች እኛ ጋር ነዉ ያሉት። ፖሊሶች የሞቱትን ሁሉን ወደ ሆስፒታል ኢያመጡ አይደለም። የሞቱት ቤተሰብ የሚታወቅ ከሆነ ወደ ቀየያቸዉ ኢየወሰዱ ነዉ።» 
የተጎዱትን ሰዎች ማንነት እና እድሜያቸዉን ዶክተሩ ተናግረዋል፤ «ሕይወታቸዉ ካለፈዉ ከአራቱ ዉስጥ አንዱ ጉታ ድዳ የተባለዉ የ25 ዓመት ወጣት ሲሆን ዛሬ ጠዋት ከሻክሶ መኪና ይዞ ወደ ሆስፒታል ኢየሄደ በመንገድ ላይ በአጋዚ ሃይል ከጀርባዉ መመታቱን ሰምቻለሁ። መክናዉም ተሰብሮ እዚህ ይገኛል። እኛ ጋር ቀዶ ህክምና ሊደረግለት ኢየተሞከረ ህይወቱ አልፏል። የ20 ዓመቱን አያኖ ጎበዘና የ18 ዓመቱ ተሰማ አሌምቦን  ትላንት ማታ ከምሽቱ 2 ሰዓት ላይ ፖሊሶች አምጥተዋቸው ህይወታቸው በሆስፕታሉ ዉስጥ አልፏል። አማኑኤል ደስታ የተባለዉን ደግሞ ሬሳዉን ነው ያመጡት። የቆሰሉትጋድሳ ኔንኮ፤ 20 ዓመት፤ ኮቶላ ታዩ፤ 21ዓመት፤ ማጋርሳ ባዳቻ፤ 45 ዓመት፤ ሃብታሙ ዮሃንስ፤ እድሜዉ 20፣ ኔኒቆ ሳፋይ፤ እድሜዉ 25፤ አድሱ አለማየሁ እድሜ 21 ናቸው።»

ዶክተር ጉሻ ባላኮን እያነጋገርናቸው የመሣሪያ ድምፅ ይሰሙ እንደነበረና ሰዎች ጉዳት መመታታቸውን መስማታቸዉን ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።

መርጋ ዮናስ

ሂሩት መለሰ