1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አሳሳቢው የኤድስ አስተላላፊ ተኀዋሲ ስርጭት

እሑድ፣ መስከረም 21 2010

የኤድስ አስተላላፊ ተኀዋሲው ስርጭት ካለፉት ጥቂት ጊዚያት ወዲህ በኢትዮጵያ እንደገና በመስፋፋት ላይ መሆኑ ተሰምቷል። ብሔራዊው የ ኤች አይ ቪ ኤድስ መቆጣጠሪያና መከላከያ ጽህፈት ቤት እንዳስታወቀው፣ ስርጭቱ ወረርሽኝ የሚባልበት አሳሳቢ ደረጃ ደርሷል።

https://p.dw.com/p/2kzaE
Symbolbild HIV-Virus
ምስል picture-alliance/AP Photo/C. Goldsmith

ውይይት፦ አሳሳቢው የኤድስ ስርጭት

ኤች አይቪ ኤድስ አሁንም በኢትዮጵያ አሉ ከሚባሉት ዋነኞቹ የጤና ተግዳሮቶች አንዱ ነው።  እርግጥ፣ በስርጭቱ መስፋፋት አንፃር የመጀመሪያው ፖሊሲ በ1990 ዓም ገቢራዊ ከሆነ እና በሽታውን የሚያስተላልፈው ተኀዋሲ በደማቸው የሚገኙ  ሰዎችን የመንከባከቡ እና ነፃ ህክምና አገልግሎት የመስጠቱ፣ እና ሰዎች ራሳቸውን መከላከል የሚችሉበት ምላሽ በ1997 ዓም መሰጠት ከጀመረ ወዲህ የተኀዋሲው ስርጭት በጉልህ ቀንሶ ነበር። ግን ካለፉት ጥቂት ጊዚያት ወዲህ የተኀዋሲው ስርጭት እንደገና በመስፋፋት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን  በብሔራዊ ኤች አይ ቪ መቆጣጠሪያና መከላከያ ጽህፈት ቤት የብሔራዊ ኤች አይ ቪ መቆጣጠሪያና መከላከያ ጽህፈት ቤት አስታውቋል።  

AIDS Schleife Symbolbild Flash-Galerie
ምስል picture-alliance/ dpa / Fotomontage: DW

በብሔራዊ ኤችአይቪ መቆጣጠሪያና መከላከያ ጽህፈት ቤት ዘገባ መሰረት፣ ባለፈው ዓመት ብቻ 27,000 ሰዎች ከተኀዋሲው ጋር እንደሚኖሩ  ተመዝግቧል።በአሁኑ ጊዜም በመላይቱ ሀገር ከተኀዋሲው ጋር የሚኖረው ሰው ቁጥር ቢያንስ 718,000 እንደሆነ ይገመታል።እርግጥ፣ ከ2000 ዓም ጋር ሲነፃፀር አዲስ ከተኀዋሲው ጋር የሚኖረው ሰው ቁጥር በ90% ቀንሷል።  በኤድስ በያመቱ እስከ 20,000 ሰው እንደሚሞት ነው የተነገረው። የኤድስ አስተላላፊ ተኀዋሲ ስርጭት ባንዳንድ አካባቢ ቅናሽ ቢያሳይም፣ በተለይ በአዲስ አበባ፣ በሐረሪ፣ እና በድሬዳዋ፣ በጋምቤላ ከፍ ብሎ እንደሚገኝ ተገልጿል። በኢትዮጵያ የስርጭቱ መጠን በወቅቱ 1,18 ከመቶ ሲሆን፣ በዓለም ጤና ጥበቃ ድርጅት መስፈርት መሰረት የስርጭቱ መስፋፋት  መጠን ከአንድ ከመቶ ካለፈ በወረርሽኝ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ያመለክታል። ስለተኀዋሲው ስርጭት እንደገና መስፋፋት፣ ምክንያቱ እና መፍትሔው ውይይት አካሂደናል። 

አርያም ተክሌ

ተስፋለም ወልደየስ