1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አፍሪቃ ርሃብን ማስወገድ ትችል ይሆን

ሰኞ፣ መጋቢት 2 2005

መልካሙ ዜና አፍሪቃዉያን መንግስታት፤ ለጋሾች እና የተመድ ለአፍሪቃ ግብርና ዳግም ትኩረት ሰጥተዋል። ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ያህል በከተሞች ኢንዱስትሪዎችን በማስፋፋት ተጠምደዉ ቆይተዋል። በዚህ መሀል ግብርናዉ ችላ ተብሎ ነበር። ።

https://p.dw.com/p/185mE
ምስል picture alliance/africamediaonline

ፖለቲከኞች የነቁት የምርት ገበያዉ ሲዛባ እና በጎርጎሮሳዊዉ 2008ዓ,ም የምግብ እህል ዋጋ ቀዉስ ተከስቶ በዚሁ ምክንያት ረሃብ ሲከተል ነዉ። ከዚህ በመነሳት የጀመርን የልማት ተራድዖ ሚኒስቴር ግብርና ላይ ያተኮረ ስልታዊ ረቂቅ እቅድ አዘጋጅቷል። አፍሪቃ ዉስጥ 900 ሚሊዮን ህዝብ ማለትም ከአጠቃላይ ኗሪዎች 90 በመቶዉ የሚሆነዉ በግብርናዉ ዘርፍ የተሰማራ ነዉ።

Klimawandel Folgen Heuschrecken Mauritanien Flash-Galerie
ምስል AP

የአፍሪቃ የግብርና ይዞታ ምን ምን ማድረግ ይችላል?

ግብርና ማለት ህይወት ነዉ። በዓለማችን ከስምንቱ አንዱ በቂ ምግብ አያገኝም። አብዛኛዉ የሚራበዉ ህዝብ የሚገኘዉ ደግሞ በደቡብ እስያና ከሰሃራ በስተደቡብ በሚገኙ የአፍሪቃ ሐገራት ነዉ። ቁጥሩ ያሳስባል። ዶቼ ቬለ በተለያዩ መገናኛ ዘዴዎቹ «አፍሪቃ ርሃብን ማስወገድ ትችላለችን?» በሚል ጥቅል ርዕሥ የአፍሪቃን የግብርና አማራጭ እድሎችና ተግዳሮቶችን ቃኝቷል። አፍሪቃ በክፍለ ዓለሙ ዉስጥ ረሃብን አጥፍታ በዚያዉ ቁጥሩ እያደገ የሄደዉን የዓለም ህዝብ የምግብ ፍላጎት ማሟላት ትችላለች? ወይም አፍሪቃ ራሷን መግባ ለዉጭ ገበያ ምግብ ማቅረብ ይሆንላታል? በምስራቅና በምዕራብ አፍሪቃ ያደረግነዉ ጥናት እንዲሁም በጀርመን የኬሚካል ቤተሙከራዎች የተደረገዉ ምርምር፤ ፖለቲከኞቿ እና ለጋሾች በጋራ የሚንቀሳቀሱ ከሆነ ይሕ እንደሚቻል አመላክቷል።

የመዋዕለ ንዋይ ፍሰትን ያለማበረታታት፤ መጥፎዉ ዜና ይቀጥላል፤ በበርካታ የአፍሪቃ ሀገሮች ስለገበሬዉ የሚሰጠዉ አስተያየት ከወሬ የዘለለ አይደለም። ገበሬዎች የራሳቸዉን ፍላጎት አሟልተዉ ትርፍ ሊያመርቱ የሚችሉበት ሁኔታ አልተመቻቸም። ለምሳሌ ኢትዮጵያ፤ ወደዘጠና ሚሊዮን ከሚጠጋዉ ህዝቧ 85 በመቶዉ ኑሮዉ በግብርና ላይ የተመሠረተ ነዉ።

Agroökosysteme in Asien und Afrika
ምስል IWMI/Comprehensive Assessment

ሆኖም ግን በማርክሳዊ ርዕዮተዓለም የተቃኘዉ ፈላጭ ቆራጭ መንግስት የመሬትን የግል ይዞታነት አይፈቅድም። ሌላዉ ቀርቶ በሊዝ መሬት የሚገዙትም የራሳቸዉ ለመሆኑ እርግጠኞች አይደሉም። ገበሬዎች የአፈር መከላትን ተከላክለዉ በአነስተኛ መሬታቸዉ ላይ አቅማቸዉን እንዳያዉሉ ያን ያህል አይበረታቱም። በተቃራኒዉ ከድህነት አዙሪት የማያወጧቸዉን ዉድ የሆኑ የእህል ዘሮችና ፀረተባይ መድሃኒቶችን ይይዛሉ። ይህም ምርትን ቀንሶ የገበዎቹን እዳ ይጨምራል።

ዛሬም የአፍሪቃ የንግድ ባንኮች ለገበሬዎች ብድር አይፈቅዱም። ስለዚህ ለዘመናት የቆየዉን ሞፈርና ቀንበር የበለጠ ገቢ ሊያስገኝ በሚችለዉ በዘመናዊ የማረሻ ስልት ለመቀየር አይቻልም። በ21ኛዉ ክፍለ ዘመን አብዛኞቹ ለገበያ በቂ እድል አላገኙም። በዝናብ ወቅት በአቅራቢያ ወደሚገኙ ገበያዎች ለመሄድ እንኳ መንገዱ አያመችም። አፍሪቃ ዉስጥ ምርትን ወደገበያ በማድረስ ሂደት ሃምሳ በመቶዉ የሚሆነዉ በስብሶ ከጥቅም ዉጭ እንደሚሆን ጥናቶች ያመለክታሉ። ይህ ተቀባይነት የሌለዉ መጠን ነዉ። ይህና መሰል አስከፊ ሁኔታዎች ዝርዝር እየረዘመ የሚሄድ እንጂ የሚገታ አይደለም።

የኢንዱስትሪ መስፋፋት አፍሪቃ ዉስጥ ያለግብርናዉ ዘርፍ ብቻዉን የሚሄድ አይደለም። የዶቼ ቬለ የምርምር ዘገባ እንዳመለከተዉ የገበሬዎችን ምርታማነትና የሰብሉን ዘር ለማሳደግ የሚጠይቀዉ አነስተኛ ጥረት ነዉ። መለስተኛ ወይም አነስተኛ መስኖ፣ ሰብል ማፈራረቅ፤ እንዲሁም ተፈጥሮዉን የጠበቀ የአስተራረስ ስልት መከተል ሁኔታዉን ለማሻሻል ከሚያስፈልጉት ጥቂቶቹ ናቸዉ።

Afrika moderne Landwirtschaft Reis Ernte in Togo
ምስል picture alliance/Yvan Travert/akg-images

ይህ ማለት ግን የኢንዱስትሪ መስፋፋት ከግብርናዉ መሻሻል ጋ የሚቃረን ነዉ ማለት አይደለም። ይልቁንም አንዱ ካለሌላዉ የሚከናወን እንዳልሆነ የሚያሳይ ነዉ። የአፍሪቃ ኢንዱስትሪዎች ጥሬ እቃዎችን ለአገልግሎት አጠናቀዉ ወደገበያዉ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፤ የአይቮሪኮስት ጥሬ ምርት ካካኦ አቢዣን እንጂ ሃምበርግ መጥቶ ለገበያ መዘጋጀት አይኖርበትም። በተመሳሳይ የአፍሪቃ መንግስታትና ለጋሾቻቸዉ የአፍሪቃን የምግብ ምርታማነት ለማሳደግ በእኩል ደረጃ የሚያገናኛቸዉ ትስስር መመስረት ይኖርባቸዋል። ለዚህም እድሉ የተመቻቸ ነዉ። በጎርጎሮሳዊዉ 2011ዓ,ም ቱኒዚያ ዉስጥ በተራቡ ወገኖች የተነሳዉ አመፅ ፓለቲከኞቹን ከመንበራቸዉ ገልብጦ ወደሰሜን አፍርቃ ብሎም ወደአረቡ ዓለም ሲያቀና፤ የአፍሪቃን እጣ ፈንታ ወሳኞች አስጠንቅቋል። ረሃብ የብዙሃኑ የፖለቲካ መሳሪያ ሆኗል። የአዉሮጳ ፖለቲከኞችም እንዲሁ በላምፔዱዛና ማልታ በሚገኙት የስደተኛ መጠለያ ጣቢያዎች ረሃብ አፍሪቃ ዉስጥ ምን እያደረገ እንደሆነ አስተዉለዋል። ወቅቱ ለአፍሪቃ ግብርና አዲስ ዉል እንዲደረስ ያመቻቸ ይመስላል።

ሉድገር ሻዶምስኪ

ሸዋዬ ለገሠ

ነጋሽ መሐመድ