1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አወዛጋቢው የካታሎንያ የመንገጠል

ማክሰኞ፣ መስከረም 30 2010

የካታሎንያ መሪዎች የግዛቲቱን ነፃነት ማወጃቸው እንደማይቀር ደጋግመው እየተናገሩ ነው። ዛሬ ለግዛቲቱ ምክር ቤት ንግግር የሚያደርጉት የካታሎንያ መሪ ካርሌስ ፕዊጂደሞንት ነጻነት ሳያውጁ አይቀርም የሚል ግምት አለ። መንግሥት ደግሞ ነጻነት የሚታወጅ ከሆነ ህግና ዴሞክራሲን ለማስከበር የበኩሉን እርምጃ መውሰዱ እንደማይቀር እየዛተ ነው።

https://p.dw.com/p/2lbS3
Spanien Carles Puigdemont Ankunft im Parlament in Barcelona
ምስል picture-alliance/Zumapress/M. Oesterle

የስፓኝዋ ግዛት ካታሎንያ፣ መገንጠልን መምረጧ ማወዛገቡ ቀጥሏል። መንግሥት ግዛቲቱ ነጻነቷን የምታውጅ ከሆነ እርምጃ እወስዳለሁ ሲል አስጠንቅቋል። የአውሮጳ ህብረትም ለካታሎንያ ነጻነት ድጋፉን እንደነፈገ ነው።የዛሬው አውሮጳ እና ጀርመን ዝግጅታችን በካታሎንያ የመንገጠል ጥያቄ እና በአውሮጳ ህብረት አቋም ላይ ያተኩራል።ለቅንብሩ ኂሩት መለሰ
ከ10 ቀናት በፊት በስፓኝዋ ግዛት በካታሎንያ በተካሄደ ህዝበ ውሳኔ 90 በመቶ የሚሆን የግዛቲቷ ህዝብ ከስፓኝ መነጠልን ደግፎ ድምጹን ከሰጠ ወዲህ የግዛቲቱ መሪዎች እና የስፓኝ መንግሥት ውዝግብ ተባብሷል። የካታሎንያ መሪዎች የግዛቲቱን ነፃነት ማወጃቸው እንደማይቀር ደጋግመው እየተናገሩ ነው። ዛሬ ለግዛቲቱ ምክር ቤት ንግግር የሚያደርጉት የካታሎንያ መሪ ካርሌስ ፕዊጂደሞንት ነጻነት ሳያውጁ አይቀርም የሚል ግምት አለ። መንግሥት ደግሞ ነጻነት የሚታወጅ ከሆነ ህግና ዴሞክራሲን ለማስከበር የበኩሉን እርምጃ መውሰዱ እንደማይቀር እየዛተ ነው። በአውሮፓ ህብረት ተሰሚነት ያላቸው ጀርመን እና ፈረንሳይ ለስፓኝ አንድነት ድጋፋቸው በመስጠት ሁለቱ ወገኖች ከዛቻ ወደ ውይይት እንዲመለሱ እያሳሳቡ ነው። ከስፓኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርያኖ ራጆይ ጋር ባለፈው ቅዳሜ ስለቀውሱ የተናነጋገሩት የጀርመን መራኂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ለስፓኝ አንድነት ድጋፋቸውን ገልጸው ውይይቱም እንዲካሄድ አበረታተዋል። ፈረንሳይ በበኩልዋ ካታሎንያ ነጻነት የምታውጅ ከሆነ ግዛቲቱ የአውሮጳ ህብረት አባል መሆን እንደማትችል አስጠንቅቃለች። እንደ ጀርመን ሁሉ ፈረንሳይም ቀውሱ በውይይት መፈታት አለበት ነው የምትለው። በካታሎንያ ጉዳይ ጣልቃ አልገባም የሚለው የአውሮጳ ህብረትም ቀውዝግቡ በውይይት እንዲፈታ ዛሬ ሃሳብ አቅርቧል። የአውሮጳ ህብረት ኮሚሽን ቃል አቀባይ አሌክሳንደር ቪንተርሽታይን።
 «ጉዳዩ የሚመለከታቸው ወገኖች በሙሉ ፍጥጫውን አቁመው በተቻለ ፍጥነት ወደ ውይይት እንዲመለሱ ጥሪ እናቀርባለን። እንዳልነው አመጽ ፍጹም የፖለቲካ መሣሪያ ሊሆን አይችልም። የስፓኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርያኖ ራጆይ ይህን ጥንቃቄ የሚጠይቅ ሂደት የስፓኝን ህገ መንግሥት እና የዜጎችን  መሠረታዊ መብቶች  ሙሉ በሙሉ በማክበር ችግሩን የመፍታት አቅም አላቸው ብለን እንተማመንባቸዋለን።»  
ከዚህ ቀደም ነጻነታቸውን ላወጁ አንዳንድ የአውሮጳ ሀገራት ግዛቶች እውቅን ሲሰጥ እና ሲደግፍ የቆየው እና ከመካከላቸውም የተወሰኑትን አባል ያደረገው የአውሮጳ ህብረት በካታሎንያ ጉዳይ ጣልቃ አልገባም ፣ነጻነትዋን ብታውጅም የህብረቱ አባል ልትሆን አትችልም ማለቱ እያጠያየቀ ነው። ህብረቱ ከሰርብያ ተገንጥላ የዛሬ 9 ዓመት ነጻነትዋን ላወጀችው ለኮሶቮ እውቅና መስጠቱ የቤልግሬድን መንግሥት ያስቆጣ እርምጃ ነበር። የቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ ግዛቶች ሲበታተኑም ህብረቱ ድጋፉን ሰጥቷል። ይህ ርስ በርሱ የሚቃረን አቋም አይደለምን? ዶቼቬለ ያነጋገራቸው ፍራንክፈርት ጀርመን የሚኖሩት የህግ ባለሞያ እና የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ዶክተር ለማ ይፍራሸዋ አዎ ይቃረናል በማለት ነው አስተያየታቸው መስጠት የጀመሩት
የህግ የበላይነት እና የዜጎችም ሆነ የውጭ ዜጎች ሰብዓዊ መብቶች የሚከበርባቸው የአውሮጳ ሀገራት የካታሎንያን ነጻነት የማይደግፉበት ምክንያት አላቸው ይላሉ ዶክተር ለማ።
የስፓኝ መንግሥት እንደሚለው የካታሎንያ ግዛት ነጻነትዋን ካወጀች የግዛቲቱን መንግሥት እስከ ማውረድ እና አዲስ አካባቢያዊ ምርጫ እስከ መጥራት የሚደርስ እርምጃ ሊወስድ እንደሚችል አስታውቋል። ፕዊጂደሞንት በነጻነት እወጃው የሚገፉ ከሆነ የመታሰር እጣ ሊገጥማቸው እንደሚችል «የህዝብ ፓርቲ» የተባለው የስፓኝ ገዥ ፓርቲ ቃል አቀባይ አስጠንቅቀዋቸዋል። ቃል አቀባይ ፓብሎ ካሳዶ ታሪክ እንዳይደገም ሲሉ በሰጡት መግለጫ ነጻነት የሚያውጀው ከዛሬ 83 ዓመት በፊት እንደሆነው ለእስር እንዳይደረግ ሲሉ አሳስበዋል፤ በጎርጎሮሳዊ 1934 የካታሎንያን ግዛት ነጻነት ካወጁ በኋላ የታሰሩትን እና ከ6 ዓመት በኋላም በቀኝ ክንፉ አምባገንነን ፍራንሲስኮ ፍራንኮ የተገደሉትን ሉዊስ ኮምፓኒስን በማስታወስ። በዶክተር ለማ አስተያየት ይህ የሚያዋጣ መንገድ አይደለም። ከዚያ ይልቅ እንደ ዶክተር ለማ የህዝቡን ጥያቄ ለመመለስ መፍትሄው መነጋገር እና መወያየቱ ነው።
የካታሎንያ ግዛት እገነጠላለሁ ካለች በኋላ በግዛቲቱ ላይ ከየአቅጣጫው የተለያዩ ዛቻዎች ተሰንዝረዋል። አንዳንድ እርምጃዎችም ተወስደዋል። እነዚህም መቃቃሩን የሚያባብሱ እንጂ የሚያቃላሉ አይደለም የሚሉት ዶክተር ለማ ሊሆን ይገባል የሚሉትን ገልጸዋል።
የስፓኝ  ጠቅላይ ሚኒስትር ማርያኖ ራጆይ እንዳሉት መንግሥታቸው የካታሎንያን የመገንጠል እርምጃ ለማስቆም የተቻለውን ሁሉ ያደርጋል። ካታሎንያዎች ዛሬ ከሦስት እርምጃዎች አንዱ ሊወስዱ ይችላሉ ተብሎ ይጠበቃል። ተግባራዊ የማይሆን ሙሉ ነጻነት እወጃ፣ ወይም ጭርስኑ ነጻነትን አለማወጅ አለያም ከማድሪድ መንግሥት ጋር አዲስ ንግግር ለማካሄድ ጥሪ ማድረግ። ውሳኔያቸው ዛሬ ይታወቃል።

Spanien Madrid Demonstration gegen Unabbhähigkeit Kataloniens
ምስል Getty Images/AFP/J. Soriano
Spanien 'Für die Einheit'-Kundgebung in Barcelona
ምስል Getty Images/AFP/L. Gene

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ