1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዶክተር አበበ ኪቢ ገመቹ 

ማክሰኞ፣ መጋቢት 10 2011

ዶክተር አበበ ከዛሬ አራት ዓመት ወዲህ በደቡብ ምዕራብ ጀርመኑ በካይዘርስላውተርን ከተማ በሚገኘው« ቬስትፋልስ ክሊኒኩም ካይዘርስላውተርን»አጠቃላይ ሆስፒታል የልብ ቀዶ ህክምና አገልግሎት እየሰጡ ነው። የልብ ቀዶ ሐኪም ከመሆናቸው በፊትም በዚህ እና በሌሎችም ሆስፒታሎች ውስጥ አገልግለዋል።

https://p.dw.com/p/3FK4J
Abebe Kibi Gemechu
ምስል privat

ኢትዮጵያዊዉ የሕክምና ባለሙያ በጀርመን


በተለያዩ ምክንያቶች ከሀገራቸው ከተሰደዱ ኢትዮጵያውያን መካከል በየሚገኙባቸው ሀገራት በተሰማሩባቸው የስራ መስኮች ስኬታማ ለመሆኑ የበቁ ኢትዮጵያውያን ይገኛሉ። በዛሬው አውሮጳ እና ጀርመን ዝግጅታችን የምናስተዋውቃችሁ የሕክምና ባለሞያ ናቸው። ሬ በአውሮጳ እና ጀርመን ዝግጅታችን የምናስተዋውቃችሁ እንግዳ ፣ዶክተር አበበ ኪቢ ገመቹ  ከኢትዮጵያ ወደ ጀርመን የመጡት የዛሬ 14 ዓመት ነው። የቋንቋ ትምሕርት እድል አግኝተው ነበር ያኔ ርዕሰ ከተማ በርሊን የመጡት። ቋንቋ እየተማሩ የጥገኝነት ማመልከቻ አስገቡና ባልጠበቁት ሁኔታ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተቀባይነት አገኙ። ይህ እድልም የልጅነት ምኞታቸውን ለማሳካት ምቹ ሁኔታ ፈጠረ። ህክምና የመማር ፍላጎት ነበራቸውና ደቡብ ምዕራብ ጀርመን ለሚገኘው ለሃይድልበርግ ዩኒቨርስቲ አመልክተው ተቀባይነት አገኙ። እዚያም ለ7 ዓመታት የህክምና ትምሕርት ተከታተለው ተመረቁ ። የዶክተር አበበ ምኞት ሕክምና ማጥናት ቢሆንም በተለይ ቀልባቸው ያረፈው የልብ ቀዶ ህክምና ላይ ነበር። የ7ቱን ዓመት ትምሕርት ከጨረሱ በኋላም በዚሁ ላይ ያተኮረ ትምሕርት ተከታትለው የልብ ቀዶ ሐኪም ለመሆን በቁ። ዶክተር አበበ ህክምና የመማር ፍላጎቱ ያደረባቸው የመለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪ ሳሉ አንስቶ ነው። ያኔ በልጅነት እድሜያቸው ያዩት በዚህ ሞያ ለመሰማራት  ምክንያት ሆነኝ ይላሉ።የልብ ቀዶ ህክምናን ያጠኑትም በምክንያት እንደነበረ ይናገራሉ። 
ዶክተር አበበ   ከዛሬ አራት ዓመት ወዲህ በደቡብ ምዕራብ ጀርመኑ በካይዘርስላውተርን ከተማ ውስጥ በሚገኘው «ቬስትፋልስ ክሊኒኩም ካይዘርስላውተርን» በተባለው አጠቃላይ ሆስፒታል ውስጥ የልብ ቀዶ ህክምና አገልግሎት እየሰጡ ነው። የልብ ቀዶ ሐኪም ከመሆናቸው በፊትም በዚህ እና በሌሎችም ሆስፒታሎች ውስጥ አገልግለዋል።
በጀርመን በህክምና ሥራ ውስጥ በተሰማሩባቸው ጊዜያት ብዙ አስተማሪ አስደሳች እና አሳዛኝም ገጠመኞች እንዳሏቸው ዶክተር አበበ ተናግረዋል። ከመካከላቸው እጅግ የተደሰቱበትን እንዲሁም ያዘኑበትን አካፍለውናል።ሰላሴ ገብረጉራቻ ከተማ የተወለዱት ዶክተር አበበ የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በዚሁ ከተማ ነው የተማሩት። መለስተኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርታቸውን ደግሞ አዲስ አበባ በሚገኙት በአርበኞች በኢትዮጵያ ትቅደም እና በእንጦጦ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርትቤቶች ነው የተከታተሉት። ከፍተኛ ትምሕርታቸውን በውጭ ሀገር የመማር ምኞታቸውን አሳክተው ፣የልብ ቀዶ ጥገና ሐኪም ለመሆን የበቁት ዶክተር አበበ የስኬታቸውን ሚስጥር የዓላማ ጽናት መሆኑን ይናገራሉ።  
በተለይ ጀርመን በስደት ለመጡ ወጣት ኢትዮጵያውያን ከርሳቸው ተሞክሮ በመነሳት የሚሰጡት ምክር አላቸው።
ዶክተር አበበ በአሁኑ ጊዜ ከሙያ ባልደረባቸው ጋር የግል ክሊኒክ ለመክፈት በዝግጅት ላይ ናቸው። ምናልባትም ከ6 ወር በኋላ ይከፈታል ብለው ይጠብቃሉ። ያም ሆኖ የዶክተር አበበ የወደፊት እቅድ እዚሁ ጀርመን መቆየት ብቻ አይደለም። ሀገራቸው ተመልሰው በሙያቸው የማገልገል ሃሳብም አላቸው። ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ዶክተር አበበ ሥራቸውን እና ማህበራዊ ህይወታቸውን አጣጥመው ለማስኬድ የተቻላቸውን ሁሉ እንደሚጥሩም ይናገራሉ። 

ኂሩት መለሰ

አዜብ ታደሰ