1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቡሀሪ 2ኛ የስልጣን ዓመት እና የናይጀሪያውያን ቅሬታ 

ማክሰኞ፣ ግንቦት 22 2009

የናይጀሪያ ፕሬዚደንት መሀማዱ ቡሀሪ ስልጣን ከያዙ ትናንት ልክ ሁለት ዓመት ሆኗቸው። የቡሀሪ የስልጣን ዘመናቸው ሊያበቃ ሁለት ዓመት ቀርቶታል።  ይሁን እንጂ፣  ቡሀሪ በዚሁ በቀራቸው የአመራር ጊዜ ውስጥ እድገት ማሳየት ያቆመውን የናይጀሪያ ኤኮኖሚያዊ ሁኔታ ማሻሻል መቻላቸውን ብዙዎች ይጠራጠሩታል።

https://p.dw.com/p/2dqNW
Muhammadu Buhari Nigeria
ምስል picture alliance/AP Photo/S.Alamba

M M T/ Bilanz_Buhari zwei jahre in Amt - MP3-Stereo

በጎርጎሪዮሳዊው 2015 ዓም ነበር ናይጀሪያውያን መሀመዱ ቡሀሪን በከፍተኛ ድምጽ ፕሬዚደንት አድርገው የመረጡት። ብዙ ናይጀሪያውያን በዚያን ጊዜ ቡሀሪ ለውጥ ያስገኛሉ የሚል ትልቅ ተስፋ ነበር ያሳደሩት።  ቡሀሪ የሀገሪቱን ፣ በተለይም ፣ የሰሜን ምሥራቅ ናይጀሪያ  የፀጥታ ሁኔታ እንደያሚያሻሽሉ፣ ስር የሰደደውን ሙስና እንደሚታገሉ፣ የሀገሪቱን ኤኮኖሚም እንደሚያሳድጉ እና አዳዲስ የስራ ቦታዎችን እንደሚፈጥሩ  ቃል ገብተው ነበር። ዛሬ ከሁለት ዓመት በኋላ  ፕሬዚደንታቸው ከገቡት ቃል መካከል ስንቱን አሟልተዋል ነው የብዙ ናይጀሪያውያን ጥያቄው።  
ናይጀሪያውያን በዚህ አኳያ ቅይጥ አስተያየት ነው የሚያሰሙት። ቡሀሪ በምርጫ ካሸነፉዋቸው የቀድሞው ፕሬዚደንት ጉድላክ ጆናታን የተበላሸ ስርዓት ነበር የተረከቡት። ናይጀሪያን ከቡሀሪ በፊት ለአስራ ስድስት ዓመት የመራው የጉድላክ ጆናታን የሕዝብ ዴሞክራቲክ ፓርቲ መልካም አስተዳደርን መመሪያዎች በፍፁም አልተከተለም ።  ቡሀሪ ስልጣኑን ሲይዙ አሸባሪው ቡድን ቦኮ ሀራም በሀገሪቱ ሽብሩን አስፋፍቶ እና የሀገሪቱም ኤኮኖሚ ወድቆ በነበረበት ጊዜ ነው። የናይጀሪያ የማስታወቂያ ሚንስትር እና የመንግሥት ቃል አቀባይ ላይ መሀመድ ምንም እንኳን ቡሀሪ የጤና ችግር ቢኖራቸውም ቃላቸውን በመጠበቅ የቦኮ ሀራም ሽብር ተጠናክሮ ይታይበት በነበረው ሰሜናዊ ናይጀሪያ የፀጥታውን ሁኔታ አሻሽለዋል ሲሉ ያሞግሷቸዋል።
« ስልጣን ላይ በመጣንበት ጊዜ ፣ ፕሬዚደንቱ ቦኮ ሀራም ያገታቸው የቺቦክ ልጃገረዶችን በሙሉ ለማስለቀቅ የሚቻላቸውን ሁሉ ለማድረግ ቃል ገቡ። እንዳሉትም፣ ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ከአንድ መቶ የሚበልጡትን ማስለቀቅ ችለናል። » በፕሬዚደንት ቡሀሪ የጠቅላላ ተራማጆች ኮንግረስ ፓርቲ የሚመራው መንግሥት ሙስናን በመታገሉም ረገድ ትልቅ ስራ እየሰራ እና በወቅቱ ብዙ ጉዳዮች በፍርድ ቤት እየታዩ መሆናቸውን ይናገራል። ይህን አባባል ግን ሁሉም ናይጀሪያውያን አይቀበሉትም። ጁልያነ ኦቦሎንዬ አንዱ ነው። 
« ሰዎች የቤት ኪራያቸውን እንኳን መክፈል አልቻሉም፣ የልጆች ትምህርት ቤት ክፍያን ለማሟላት ሲታገሉም ይታያሉ። ቤተሰባችንን እንደሚገባው መመገብም አልቻልንም።»
ቼሳ ቼሳም፣ እርግጥ፣ መንግሥት በፀጥታው ዘርፍ መልካም ውጤት ማሳየቱን ቢገልጽም፣  የሕዝቡን ኑሮ ደረጃ እንዳላሻሻለ በቅሬታ ተናግሯል።

Nigeria - Heimkehr der Chibok Mädchen
ከእገታ የተለቀቁ የቺቦክ ልጃገረዶችምስል Reuters/A. Sotunde

«  የዋጋ ግሽበቱ ከፍ ብሏል። የኤኮኖሚ እድገት ስለማይታይም  የምግብ ዋጋ እየጨመረ ሄዷል።»

Nigeria Bodo Gemeinde in Ogoni Yemi Osinbajo und Amina Mohammed
የሚ ኦሲናባዦ ምስል DW/M. Bello

ምንም እንኳን የመንግሥት ባለስልጣናት ፕሬዚደንት ቡሀሪ ናይጀሪያን ወደፊት ለማራመድ ብዙ እየሰሩ መሆናቸውን ቢናገሩም፣ እንደ የፖለቲካ ተንታኝ እና በመዲናይቱ አቡጃ ዩኒቨርሲቲ መምህር ዶክተር ጋርባ ኡማር አስተያየት፣ ፕሬዚደንቱ ለረጅም ጊዜ ለህክምና በለንደን ብሪታንያ በቆዩባቸው ሁለት ወራት ገደማ የሀገር አመራሩን ስራ ያካሄዱት ምክትል ፕሬዚደንት የሚ ኦሲናባዦ ለተመዘገቡት ውጤቶች ከፍተኛ ድርሻ አበርክተዋል።  
« ምክትል ፕሬዚደንቱ መንግሥት የነደፋቸው መርሀግብሮች በታቀደው መሰረት እንዲከናወኑ አድርገዋል።  የፕሬዚደንቱ  በሀገር አለመኖር መርሀግብሮቹ በተግባር የሚተረጎሙበትን ሂደት  አላተስተጓጎለም። »
ናይጀሪያውያን አሁን እንደገና ላልታወቀ ጊዜ ለህክምና ወደለንደን የሄዱት የፕሬዚደንት ቡሀሪ የስልጣን ዘመን ይቀጥል አይቀጥል ለመወሰን ግን ገና ሁለት ዓመት መጠበቅ ይኖርባቸዋል። 

 

አርያም ተክሌ

ሂሩት መለሰ