1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የብሪክስ አባል ሀገራት ስምምነት

ሰኞ፣ ሐምሌ 23 2010

ብሪክስ በመባል በሚታወቀው ቡድን የሚጠቃለሉት ብራዚል፣ ሩስያ፣ ህንድ፣ ቻይና እና ደቡብ አፍሪቃ መሪዎች የዓለም ንግድ ድርጅት የሚያበረታታውን አንድ ሁሉን አካታች ብዙ ሀገራት አቀፍ  የንግድ ስርዕት  ለመፍጠር የሚያስችል አንድ የስምምነት ሰነድ ተፈራረሙ።

https://p.dw.com/p/32DQq
Gipfeltreffen der Brics-Staaten in Südafrika
ምስል Getty Images/M.Hutchings

«የራስን ጥቅም ብቻ ለማስጠበቅ የሚደረግ ርምጃን ማከላከል ያስፈልጋል።»

አምስቱ የብሪክስ አባል ሀገራት ደቡብ አፍሪቃ በጆሀንስበርግ ከተማ ባስተናገደችው የሶስት ቀናት ጉባዔ ላይ  ዓለም አቀፍ የንግድ ትስስርን በአንድ ድምፅ ደግፈዋል።ትብብር ለሁሉ አካታች ዕድገት እና የጋራ ብልፅግናን  የሚል አጀንዳ በያዘው አስረኛው የብሪክስ ጉባዔ የተገኙት የአምስቱ ሀገራት መሪዎች በተለይ የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ በአጋር ሀገራት ላይ ተጨማሪ ቀረጥ ለመጣል ያሰሙት ዛቻ በዓለም አቀፍ የንግድ ግንኙነት ላይ በደቀነው ስጋት አንጻር ትግላቸውን ለማጠናከር እና የራስን ጥቅም ብቻ ለማስጠበቅ የሚደረግ ርምጃን እንደሚያከላክሉ ለጉባዔው ተሳታፊዎች ግልጽ አድርገዋል። የብሪክስ አባል ሀገራት አራተኛውን የኢንዱስትሪያዊ ዓብዮትን ቢቀላቀሉ እና አዲሱን ቴክኖሎጂ ቢያስተዋውቁ ተጠቃሚዎች እንደሚሆኑም ሁሉም በአጽንዖት ተናግረዋል። በአሁኑ ጊዜ በመካሄድ ላይ ያለውን ኢንዱስትሪያዊውን ዓብዮት ችላ የሚሉ ሀገራት ለችግሮቻቸው መፍትሔ ማግኘት እንደሚከብዳቸው ደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንት ሲሪል ራማፎዛ አስጠንቅቀዋል።
« አራተኛው ኢንዱስትሪያዊ  ዓብዮት የሚያስገኘው ጥቅም በጥቂት ሀገራት እጅ ብቻ ተይዞ እንዳይቀር  ማረጋገጥ ይኖርብናል።  ሁሉን የሚያካትት ፣ የተለያዩ አካሄዶችን የሚያጎላ አሰራርን እና ትብብርን ማበረታታት አለብን። »
የሩስያው ፕሬዚደንት ብላዲሚር ፑቲንም የብሪክስ አባል ሀገራት የአራተኛውን ዓብዮት ፍሬ ሊቋደሱ እና ምርታቸውንም ሊያሳድጉ የሚችሉት አዲሱን ቴክኖሎጂ  ሲጠቀሙ ብቻ መሆኑን አስታውቀዋል።
«  በዓለም አቀፉ ንግድ ውስጥ የብሪክስ ሀገራት ልዮ ሚና ይዘዋል። ይኸው ቡድን በዓለም ገበያ ውስጥ ትልቅ ድርሻ አለው። የአምስቱ አባል ሀገራቱ ጠቅላላ ብሔራዊ ገቢ 42 ከመቶ ሲሸፍን፣  በያመቱም በ22,3 ከመቶ በማደግ ላይ ይገኛል። »
የብሪክስ ሀገራት ዜጎቻቸው በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚታየው የንግድ ሂደት ውስጥ ወሳን ሚና እንዲጫወቱ ለማስቻል የሳይንስና ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ እንዲያደርጉ ነው የቻይና ፕሬዚደንት ዢ ጂንፒንግም ያሳሰቡት።
«  የብሪክስ ዋና ዓላማ እንደሚጠቁመው፣ በአባል ሀገራት መካከል የሚኖረው የቅርብ የኤኮኖሚ ትብብር ብልፅግናን ያረጋግጣል።  ንግድን፣ ኢንቬስትመንት ማሳደግ፣ የፊናንሱን እና የኤኮኖሚውን ትስስር ትብብር በማጠናከርም ዓለም አቀፍ ንግድ ከሚያስገኘው ትርፍ የሚደርሰንን ድርሻ ማሳደግ ይኖርብናል። »
በጉባዔው ከተገኙት የአርጀንቲንያ፣ አንጎላ፣ ቱርክ፣ ሴኔጋል እና ዚምባብዌ ጋር ትብብራቸውን  እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል።

Südafrika, Johannesburg: 10.ter BRICS-Gipfel
ምስል Reuters/S. Sibeko

አርያም ተክሌ

ማንተጋፍቶት ስለሺ