1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቻይና እና የአፍሪቃ የትብብር መድረክ

ቅዳሜ፣ ነሐሴ 26 2010

በፔኪንግ የፊታችን ጎርጎሪዮሳዊው መስከረም ሶስት እና አራት የሚደረገው የቻይና አፍሪቃ የትብብር መድረክ ጉባዔ  ቻይና ከአፍሪቃ ጋር ያላትን ግንኙነት ይበልጥ እንድታጠናክር የሚረዳ ነው ተባለ።

https://p.dw.com/p/347Q8
Symbolbild chinesische Auslandshilfe in Afrika
ምስል picture-alliance/AP Photo/G. Baker

የቻይና እና የአፍሪቃ የትብብር መድረክ

የቻይና ፕሬዚደንት ዢ ጂንፒንግ በጆሀንስበርግ ደቡብ አፍሪቃ ታህሳስ 2015 ዓም ወዲህ በተደረገው ጉባዔ ላይ ከአህጉሩ ጋር ግንኙነት እንደሚያጠናክሩ መግለጻቸው ይታወሳል። ይኸው በሚቀጥለው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ቻይና የምታስተናግደው የሁለት ቀኑ ጉባዔም ትልቅ ትርጓሜ እንዳ,ያዘ የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ዋንግ ዪ አስታውቀዋል።

« የቻይና አፍሪቃ የትብብር መድረክ ጉባዔ በጣም ትልቁ ጉባዔ ነው የሚሆነው። ፔኪንግ የሚገኘው መንግሥት በትልቅ ተነሳሽነት የሚያዘጋጀው ትልቅ ዓለም አቀፍ ትርጓሜ የያዘ ጉባዔ ነው። ቻይና እና አፍሪቃ ለጋራ ስኬት እየሰሩ ነው። በጉባዔው የሚሳተፉት ሀገራት ሁሉ ተጠቃሚ የሚሆኑበት ሁኔታ ነው ያለው። አብሮ መስራቱም ሁሉን ተሳታፊ ሀገራት ይጠቅማል። »

የቻይና መንግሥት መገናኛ ብዙኃን፣ በተለይ በውጭ ሀገራት ዝግጅቶቹን በሚያስተላልፈው  በቻይና ዓለም አቀፍ የቴሌቪዥን መረብ፣ በምህፃሩ፣ ሲጂ ቲ ኤን  ከአፍሪቃ ጋር ያለውን የሀገራቸውን ግንኙነት በተመለከተ  ከጉባዔው አስቀድመው ነበር የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ የጀመረው። የምዕራብ እስያ እና አፍሪቃ ምርምር ማዕከል ባልደረባ ሼን ዢያኦሌይ እንደሚያስታውሱት፣ ቻይና ዋነኛዋ የንግድ አጋርነት ቦታ የያዘችው ከዘጠኛ ዓመታት በፊት ነበር። ከአፍሪቃ ጋር ያለውን የቻይና ግንኙነት ለማስፋፋት በምትከተለው ፖሊሲ የሀገሪቱ ፕሬዚደንት ዢ ጂንፒግ አዘውትረው አፍሪቃን  ጎብንተዋል። ዢ ጂንፒንg ከርሳቸው በፊት በነበሩት መሪዎች አንጻር አራት ጊዜ ወደ አፍሪቃ በመሄድ የተለያዩ ሀገራትን ጎብኝተዋል፣ ይህ በአፍሪቃ አኳያ የሚከተሉት ፖሊሲም ውጤት እንዳስገኘላቸው እና ከ,,አፍሪቃ ጋር ግንኑነቱ በጣም ፈጣን እና በላቀ ደረጃ በማደግ ላይ እንደሆነ  የቻይና ዓለም አቀፍ ጥናት ተቋም የአፍሪቃ አጥኚ ዜንግ አይፒንግ  አስረድተዋል።

Senegal Einweihung Wrestling Arena Xi Jinping Macky Sall
ምስል Getty Images/AFP/Seyllou

በቻይና እና በአፍሪቃ መካከል የሚካሄደው የንግድ ግንኙነት እድገት በርግጥ በጣም ከፍተኛ ነው። በተመድ የዓለም ንግድ እና የልማት ጉባዔ፣ በምህፃሩ፣ ኡንክታድ ዘገባ መሰረት፣ የአፍሪቃ እና የቻይና  የንግድ ግንኙነት በ2000 ዓም አስር  ቢልዮን ዩኤስ ዶላር ነበር፣ የንግዱ ግንኙነት መጠን አሁን ከ17 ዓመት በኋላ በሀያ እጥፍ አድጎ 200 ቢልዮን ዶላር ደርሷል፣ ቻይና በአፍሪቃ የምታደርገው ቀጥተኛ ውረታው ጎን ለጎን በጉልህ አድጓል።

 የውጭ በአንጻሩ አፍሪቃ  ከአውሮጳ እና ከዩኤስ አሜሪካ ጋር ያላት የንግድ ግንኙነት  በነዚሁ ዓመታት ውስጥ እድገት ሳያሳይ ባለበት ቆይቷል። የቻይና እና አፍሪቃውያቱ ሀገራት ትብብር በአስር ዓበይት  ዘርፎች ላይ ነው ያተኮረው። ግብርና፣ መሰረተ ልማት፣ የፊናንስንግድ እ ና ኢንቬስትመንት፣ ድህነት ቅነሳ፣ ጤና ጥበቃ፣ ኢንዱስትሪ እና ፀጥታ ይገኙባቸዋል። ይህ ትብብር ትልቅ ትርጉም ለሀገራቸው እንደያዘ  የላይቤሪያ ኤኮኖሚ እና ፊናንስ ሚንስትር አውጉስቱስ ፍሎሞ አረጋግጠዋል።

«ቻይና የአዲሱ የልማት ስልታችን ውስጥ በጣም ዋና አጋር ናት። በአዲሱ የልማት ስልት ውስጥ የመሰረተ ልማት ግንባታ ፣ የኃይል መረብ ዝርጋታ፣ እንዲሁም፣ የጤና ዘርፉን ዘመናይ የማድረጉ እቅድ ተካቷዋል።  »

የኬንያ ፕሬዚደንት ኡሁሩ ኬንያታም ከቻይና ጋር የሚደረገው ትብብር ሁሉንም እንደሚበጅ ለሲጂቲኤን በሰጡት ቃለ ምልልስ ገልጸዋል።

« የቻይና አፍሪቃ የትብብር መድረክ ጉባዔ ለተሳታፊ ሀገራት በጠቅላላ ትልቅ እድል የሚሰጥ ነው ብዬ አምናለሁ። ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርግ ሁኔታ ነው። እንደ ሀገር እና እንደ አህጉር ከቻይና ጋር ግንኙነታችንን ስንገነባ ጥሩ እድል እናገኛለን። »

የንግድ ማከላከል ፖሊሲ ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ያመለከቱት የኬንያዊው ርዕሰ ብሔር በቻይና እና በአፍሪቃ  መካከል ገበያዎች ክፍት የሚሆኑበት አሰራር የሚጀመርበትን ሀሳብ አጉልተዋል። ይሁንና፣ በኬንያታ አንጻር በላፕሲግ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሀብት መምህር ሮበርት ካፔል የቻይና ንግድ  ፖሊሲ አፍሪቃን እየጎዳ ነው ብለዋል።

ለነገሩ ኬንያታ ቻይናን መውቀስ ነበረባቸው። ምክንያቱም ቻይና በመንግሥት ድጎማ እና በሀገሯ ቱጃሮች የሚመረተውን ፣ ለምሳሌ፣ ባይስክል፣ ባትሪ፣ ሻማ ፣ ፍሪጅን የመሳሰሉ ምርቶችን  በንግድ ወደ አፍሪቃ በመላክ እና በርካሽ ዋጋ በማቅረብ የአፍሪቃን ገበያዎች እየገደለች ነው። በመሰረቱ ከቻይና ም ጋር የሚደረገው ነፃው ንግድ በአፍሪቃ ኢንዱስትሪያነት እንዳይስፋፋ ድርሻ አበርክቷል።  »

USA und China kämpfen um Einfluss in Afrika
ምስል dapd

አፍሪቃውያን መንግሥታት ኤኮኖሚያዊ እድገት ለማስገኘት ለሚያደርጉት እንቅስቃሴ የሚያስፈልገውን ብድር በተመለከተ በይበልጥ በእስያዊቱ ሀገር ቻይና ላይ ጥገኛ እየሆኑ ነው በሚል የላይፕሲኽ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሀብቱ መምህር ሮበርት ካፔል የጉዳዩን አሳሳቢነት ገልጸዋል ።

«ቻይና ለመሰረተ ልማት ለምሳሌ ከጅቡቲ አዲስ አበባ ወይም ከሞምባሳ ወደ ናይሮቢ ለሚዘረጋው የባቡር መስመር ግዙፍ ብድር ትሰጣለች። ። እነዚህ ውድ እና ብዙ ገንዘብ የሚፈጁት የመሰረተ ልማት ግንባታዎች  የሚገኘውን ብድር የሚከፍሉት ራሳቸው አፍሪቃውያኑ መንግሥታት ናቸው። ይህም ብዙዎቹን አፍሪቃውያት ሀገራት የግዙፍ ዕዳ ተሸካሚ አድርጓቸዋል።

 እንደ ካፔል አስተያየት፣ ቻይና በአፍሪቃ አኳያ እየተከተለችው ባለው ፖሊሲ በተዘዋዋሪ  መንገድ በአህጉሩ  ፖለቲካ ላይ ተፅዕኖ አሳርፋለች። ምንም እንኳን ቻይና በሀገራቱ ውስጣዊ ጉዳዮች ላይ ጣልቃ እንደማትገባ ብትናገርም፣ በሰላም ማስከበር ተልዕኮ በተሳተፈችባት በደቡብ ሱዳን፣ እንዲሁም፣ የጦር ሰፈር በተከለችባት ጅቡቲ ፖለቲካ ላይ ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ  ፖለቲካዊ ተፅዕኖ እያደረገች መሆኗን ነው ካፔል ያስታወቁት። ይህ  ተፅዕኖም ውጤት እያስገኘላት መሆኑ ከስዋዚላንድ በስተቀር ሌሎች  አፍሪቃውያን መንግሥታት ከታይዋን ጋር ያደርጉት የነበረውን ትብብር ያቋረጡበት ድርጊት በግልጽ ያሳየ ነው።  

አርያም ተክሌ/አንቶንዮ ካሽካሽ

ማንተጋፍቶት ስለሺ