የፌደራል ስርዓቱ ሊሻሻል ይገባል ተባለ
ቅዳሜ፣ ግንቦት 10 2011አሁን ያለው የፌደራላዊ መንግስት አወቃቀር ስርአት ጊዜውን እና የተለወጡ በርካታ ማህበረ ፖለቲካ እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎችን ማስተናገድ የማይችል በመሆኑ ሊሻሻል ይገባል የሚል ምክረ ሃሳብ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ተሰንዝሯል። ከተወያዮቹ መካከል የተለየ ሃሳብና አማራጭ ነው ያሉትን ሃሳብ የዘረዘሩት ፖለቲከኛው አቶ ልደቱ አያሌው ዋናው ስርአት ፌዴራላዊ ሆኖ ነገር ግን ከአሃዳዊ ስርአት በጎ አካሄዶችንም መውሰድ ያስፈልጋል ብለዋል።
አቶ ልደቱ በቀበሌ እና ወረዳ ደረጃዎች ላይ አሁን ያለው ብሄር ተኮር አወቃቀር መቀጠል አለበት ባይ ናቸው። ሆኖም በማዘጋጃ ቤት ደረጃ መደራጀት የሚችል ህዝብ ቁጥር ያላቸው ከተሞች ላይ አሃዳዊ ስርአት ሊዘረጋ እንደሚገባ አማራጭ ያሉትን አቅርበዋል። በዞን እና በክልል ደረጃ መስፈርቱ ከቋንቋ እና ማንነት በላይ ያሉ ጉዳዮችን ታሳቢ ማድረግ አለበት የሚል ሃሳብም ሰንዝረዋል።
በውይይቱ ላይ ሃገራዊ አንድነትን እና የአናሳዎችን መብት ማስከበር የሚችል፣ ሁሉም የሚሳተፍበት ኢትዮጵያን እንደኢትዮጵያ ማስቀጠል የሚችል ፌዴራላዊ ስርአት ሊዋቀር ይገባል የሚል ሃሳብ ተንጸባርቋል። የፌደራላዊ ስርዓቱ አሁን በሀገሪቱ ለሚታየው ችግር አስተዋጽኦ እንዳለው የጠቀሱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው ከህገመንግስት ጀምሮ ማሻሻያ እንዲደረግበት አሳስበዋል። የትኛው ስርዓት ይሻላል በሚለው ላይ ሁሉም ሊወያይበት ይገባልም ተብሏል።
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።
ሰለሞን ሙጬ
ተስፋለም ወልደየስ