1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ግጭት በአዳማ መጠለያ ጣቢያ

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 8 2010

በኦሮሚያ ክልል አዳማ ከተማ ከሶማሌ ክልል የተፈናቀሉ ሰዎች በሚኖሩበት መጠለያ ስፍራ በተከሰተ ግጭት በርካቶች መጎዳታቸዉ ተገለፀ።በግጭቱ ከተጎዱት መካከል የአንድ ሰዉ ህይወት መጥፋቱን የአዳማ ሆስፒታል አስታዉቋል።ግጭቱ በአካባቢዉ ነዋሪዎችና መጠለያ በሚገኙ ሰፋሪዎች መካከል መሆኑን ነዋሪዎች አመልክተዋል።

https://p.dw.com/p/339jf
Äthiopien, Adama
ምስል DW/M. Yonas Bula

Conflict in Adama - MP3-Stereo


አቶ ቤኛ ዳባ የተባሉ የአዳማ ከተማ ነዋሪ ለዶቼ ቬለ እንደገለፁት ትናንት አመሻሹ ላይ የተከሰተዉ ግጭት ካለፈዉ መስከረም ወር ጀምሮ ከሶማሌ ክልል ተፈናቅለዉ በአዳማ መጠለያ ጣቢያ በሰፈሩ ሰዎችና በአካባቢዉ ነዋሪዎች  መካከል ነዉ።ግጭቱ ሲከሰት ይህ ለሶስተኛ ጊዜ ነዉ የሚሉት ነዋሪዉ፤ በግጭቱ የተፈናቃዮቹ መጠለያ ቤቶች መቃጠላቸዉንና ሰዎች መጎዳታቸዉን ገልፀዋል።የግጭቱን መነሻ እንዲህ ነዉ የገለፁት «በትናንትናዉ ግጭት መጀመሪያ እዚህ አካባቢ የድንጋይ ማዉጣት የሚባል ነገር ነበር።እዚህ አካባቢ ያለ።በመጀመሪያም በዚህ ጉዳይ ላይ ችግር ተከስቶ መንግስት እዛ አካባቢ ያለዉ ድንጋይ እንዳይወጣ አግዶ ነበር።አሁን ደግሞ ያ ድንጋይ የማዉጣት ስራ ተፈቀደ።ሰዎች ሄደዉ የማዉጣት ነገር ነበር።ግጭቱ በዚህ ምክንያት ተከሰተ»ነዉ ያሉት።
በአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ የ3ተኛ አመት የቀዶ ጥገና ፕሬዝዳንት የሆኑት ዶክተር ዲዳ ባቱ  በግጭቱ በርካታ ሰዎች ተጎድተዉ ለህክምና ወደ ሆስፒታሉ መምጣታቸዉን ገልፀዋል። ለህክምና ከመጡ ሰዎች መካከልም የአንድ ሰዉ ህይወት መጥፋቱን አመልክተዋል።«ትንንት ተጎድተዉ የመጡ ሰዎች ነበሩ።በአጠቃላይ 36 ሰዎች ተጎድተዉ መጥተዋል።ከዚያም 26 ወንዶችና 9ኑ ሴቶች ነበሩ።አንደኛዉ ሞቶ ነዉ የደረሰዉና  አንድ ሞት ነበረ።ሌሎች  መጠነኛ ጉዳት የደረሰባቸዉ ነበሩ ።ታክመዉ በብዛት ወደ ቤት ሄደዋል።የተወሰኑት ሆስፒታል ቀርተዉ እየታከሙ ነዉ ያሉት።»ብለዋል
ወደ ሆስፒታሉ የመጡት ተጎጅዎች ሁሉም ከሶማሌ ክልል ተፈናቅለዉ የመጡና  አብዛኛዎቹም ጭንቅላታቸዉ ላይ በድንጋይ የመፈንከት አደጋ ያጋጠማቸዉ መሆናቸዉን  ዶክተሩ አብራርዋል።
እንደ አዳማ ከተማ ነዋሪዉ ገለጻ ከአንድ ወር በፊት የሰዉ ህይወት ባይጠፋም በቦታዉ ተመሳሳይ ግጭት ተከስቶ ነበር።ከዚያ ቀደም ብሎም  በአካባቢዉ በተደጋጋሚ ችግር ተከስቷል።ያምሆኖ ግን በቦታዉ የሚገኘዉ አስተዳደር በጊዜ መፍትሄ ባለመስጠቱ እዚህ ሊደርስ ችሏል ሲሉ ነዋሪዉ ተችተዋል።
ግጭቱ ከተቀሰቀ በኋላም ቢሆን የፀጥታ አካላት ሁኔታዉን ለማረጋጋት ቶሎ ወደ ቦታዉ አልደረሱምም ብለዋል። 
ስለ ጉዳዩ የአዳማ ከተማ አስተዳደርን ለማነጋገር ያደረግነዉ ጥረት አልተሳካም።

Äthiopien Somalia Vertriebene Menschen
ምስል DW/B. Girma
Äthiopien Somalia Vertriebene Menschen
ምስል DW/B. Girma

ሙሉ ቅንብሩን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነዉ ያድምጡ።

ፀሐይ ጫኔ

ኂሩት መለሰ